አሳሳቢው የጋዜጠኞች ሁኔታ በሶማልያ
ረቡዕ፣ ጥቅምት 21 2005
በሶማልያ የጋዜጠኞች ሁኔታ አሳሳቢ መሆኑን ሞቃዲሾ የሚገኘው ጋዜጠኛ መሀመድ ኦማር ሁሴይን ገlልጾዋል።
በሞቃዲሾ የተገደለው የስድሳ አንድ ዓመቱ ዋርሳም ሺሬ አዋል የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያ ብቻ ሳይሆን በሶማልያ ህብረተሰብ ዝና ያተረፈ አዝናኚም እንደነበር ጋዜጠኛ መሀመድ ኦኦማር ሁሴን ያስታውሳል።
« ከትናንት በስቲያ የተገደለው ሚስተር ዋርሳም ሺሬ አዋል ጋዜጠኛ ብቻ አልነበረም፡ ገጣሚ፡ ዘፋኝ እና አቀናባሪም ነበር። በቀድሞው የሲያድ ባሬ መንግሥት ዘመን የሶማልያ ክሬሰንት ዋች ባንድ አባልም ነበር። የዚያድ ባሬ መንግሥት ከተገረሰሰ በኋላ አዋሌ ኩልሚየ ለተባለው ያካባቢ ራድዮ ይሰራ ነበር። እና በሀገሪቱ ሰላም እና መረጋጋት ይውረድ የሚል መልዕክት የያዘ ተከታታይ የራድዮ ድራማ አዘጋጅቶ ይተላለፍ ነበር። እና አንዳንድ አሸባብን የመሳሰሉ ቡድኖች በመልዕክቱ አልተደሰቱም። »
የአዋሌ ዝግጅቶች በሶማልያ መንግሥት አንፃር የሚዋጋው የአሸባብ አመራር የእሥላማዊውን ሕግ አላግባብ በስራ ላይ አውሎዋልም በሚል ይተቹ እንደነበር ተገልጾዋል። እና በተለይ በወጣቱ ትውልድ ዘንድ ተወዳጅ የነበረው ዋርሳሜ ሺሬ አዋሌ እቤቱ ደጃፍ ቆሞ ሳለ ሁለት ወጣቶች ጠጋ ብለው ማንነቱን ካረጋገጡ በኋላ ተኩሰው ገድለውት እንደሸሹ ነው ጓዶቹ የገለጹት።
እንደመሀመድ ኦማር ሁሴይን አስተያየት፡ በተለይ ባለፉት ዓመታት ሶማልያውያን ጋዜጠኞች ስራቸውን የሚያከናውኑበት ሁኔታ እጅግ አደገኛ እየሆነ መጥቶዋል። በሶማልያ ጋዜጠኞች ለሚገደሉበት ድርጊት መሀመድ ኦማር ሁሴን ምክንያቱን ሲያስረዳ፡
« ጋዜጠኞቹ የሚያቀርቡዋቸው ስራዎቻቸው አንዱን ወገን ሲያስደስቱ ሌላውን ያስቆጣሉ። የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ወይም የፕሬስ ሰራተኞች የሚያቀርቡዋቸው አስተያየት ሁሌ የሚያስቆጣው ወገን ወይም ግለሰብ ይኖራል። እና ቅር የተሰኘው ግለሰብ ወይም ወገን ያንን ጋዜጠኛ ፈልጎ ለማግኘትና ለመግደል ይሞክራል። »
በአሳሳቢ ሁኔታ ላይ የሚገኙት ሶማልያውያን ጋዜጠኞች ከመንግሥትም ሆነ ከብሔራዊ የጋዜጠኞች ህብረት አንዳችም ከለላ አይደረግላቸውም። ውጊያ ከሚካሄድባቸው አካባቢዎች ዘገባ የሚያቀርቡ ጋዜጠኞች እንኳን አስፈላጊው ከለላ ይጎድላቸዋል። ለጋዜጠኞች መብት የሚሟገቱ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችም ቢሆኑ በጋዜጠኞቹ ላይ የሚፈጸመውን ግድያ ከማውገዝ ያለፈ ድጋፍ እንደማያደርጉ ጋዜጠኛው መሀመድ ኦማር ሁሴን ይናገራል።
« ለነገሩ የቢላ ስለት እያረፈብን ነው። ብቻችን ነው ያለነው። እጅግ አስጊ በሆነ ሁኔታ ላይ ነው የምንገኘው። ያም ቢሆን ግን ጋዜጠኞች በጣም ቆራጥና ለህብረተሰቡ ማበርከት ያለባቸውን ስራ ተስፋ ሳይቆርጡ እስከመጨረሻው ለማቅረብ ይንቀሳቀሳሉ። »
ባለፉት አሥር ወራት ከተገደሉት ጋዜጠኞች መካከል ለአሥሩ አሸባብ ተጠያቂ መሆኑን ቢገልጽም፡ ጋዜጠኛ መሀመድ ኦማር ሁሴን እንደሚለው፡ እስካሁን አንድም ሰው ከግድያው ጋ በተያያዘ የታሰረም ሆነ ለፍርድ የቀረበ አንድም ሰው የለም።
« መንግሥት ተጠያቂዎቹን ፈልገው ለፍርድ እንደሚያቀርብ ሁሌ ይናገራል። ግን እስካሁን ለአንድ ጋዜጠኛ ግድያ እንኳን ተጠያቂ የሆነ አንድም ሰው ለፍርድ አልቀረበም። »
አርያም ተክሌ
ሂሩት መለሰ