ትኩረት የሚሻው የአዕምሮ ጤና
ማክሰኞ፣ ነሐሴ 13 2006የአእምሮ ጤና ትኩረት ከተነፈጋቸዉ የህመም ዓይነቶች ዉስጥም እንደሚደመር ነዉ የተገለጸዉ። ባለፈዉ ሳምንት ኢትዮጵያ ዉስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ የአዕምሮ ጤናን የተመለከተ ሲምፖዚየም ተካሂዷል። በዓለም 450 ሚሊዮን ሰዎች ለአእምሮ ወይም ለስርዓተ ነርቭ መዛባት ችግር የተጋለጡ መሆናቸዉን መረጃዎች ያመለክታሉ። የዓለም የጤና ድርጅት እንደሚለዉ ከእነዚህ ሁለት ሶስተኛ እጅ የሚሆኑት ምንም ዓይነት ህክምና እንደማይፈልጉ ይገልጻል። ህክምናዉን የማይፈልጉትበት ምክንያት ግን ከእነሱ ፈቃድ የመጣ ብቻ አይደለም፤ በመገለል በአድልዎና ችግሩን ከመባባሱ አስቀድሞ ሊደረግ የሚገባዉ የመከላከል ርምጃ በመዘንጋቱ መሆኑን የዓለም የጤና ድርጅት ያስገነዝባል።
አዕምሮ ጤና ካልሆነ ጤና አለኝ ማለት እንደማይቻል የሚያመላክት ሀረግን መመሪያ ያደረገዉ የዓለም የጤና ድርጅት ካለፉት ሁለት ዓመታት አንስቶ እስከመጪዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 2020 ድረስ በዘርፉ የሚሰጠዉ ህክምና በተወሰነ ቦታ ብቻ ሳይሆን በየሃኪም ቤቱ እንዲሆን የማስቻል ጥረትን አጠናክሮ ለመቀጠል ያለመ ነዉ። ከዓመታት በፊት የአዕምሮ ጤናን አስመልክቶ ደቼ ቬለ ያነጋገራቸዉ በኢትዮጵያ የዘርፉ አንጋፋ የህክምና ባለሙያ ዶክተር መስፍን አርአያ የዚህን አስፈላጊነት ሲገልጹ፤ በአማኑኤል ሆስፒታል ብቻ ህክምናዉ መሰጠቱ ለዚህ ችግር የተጋለጡ ወገኖች ለትኩረት ብሎም ለመነጠል እንደሚዳርግ ማስገንዘባቸዉ ይታወስ ይሆናል። ያንን ለማስቀረትም በአዲስ አበባ ቅዱስ ጳዉሎስን ጨምሮ በተለያዩ ሃኪም ቤቶች፤ በጅማ፤ በአዳማ፣ በመቀሌ፣ በሐረርና ሀዋሳም የስነልቡና ባለሙያዎች ተመድበዉ መሠራት መጀመሩን ገልጸዉ ነበር። በወቅቱ ኢትዮጵያ ዉስጥ ከ80 ሚሊዮን በላይ ለነበረዉ ህዝብ ያሉት የዘርፉ ሃኪሞች ከአርባ እንደማይበልጡ ዶክተር መስፍን ገልጸዉልን ነበር አሁንስ ስንት ደርሰዉ ይሆን? ዶክተር መስፍን አርአያን ጠይቄያቸዋለሁ፤ ከድምፅ ዘገባዉ ያድምጡ፤
ሸዋዬ ለገሠ
ነጋሽ መሐመድ