ቤጂንግ፤ የአዉሮጳ ኅብረትና የቻይና ጉባኤ
ማክሰኞ፣ የካቲት 6 2004ማስታወቂያ
ቤጂንግ ላይ የአዉሮጳ ኅብረትና የቻይና ጉባኤ ከተካሄደ በኋላ ዌን ለጋዜጠኞች እንዳመለከቱት አገራቸዉ ግዙፏ የንግድ አጋሯ አዉሮጳ መረጋጋቷንና ብልፅግናዋን አጠናክራ እንድትቀጥል እንደምትሻም ገልጸዋል። የአዉሮጳ ልዑካን በጉባኤዉ ላይ የቻይና ተሳትፎ የገጠማቸዉን የፋይናንስ ቀዉስ ለማረጋጋት ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ለማስረዳት ጥረት ማድረጋቸዉ ተገልጿል። የአዉሮጳ ኅብረት ፕሬዝደንት ኸርማን ፋን ሮምፖይ የጉባኤዉን ዉሎ እንዲህ ገልፀዉታል፤
«በተደጋጋሚ ለአዉሮጳ ንግድና የአዉሮጳ ኩባንያዎች የተደላደለ የገበያ ሁኔታና የተሻለ ገበያ ማመቻቸት እንደሚያስፈልግ፤ የመዋዕለ ንዋይ ከለላና የአዕምሮ ንብረት ጥበቃና ከለላን የሚመለከት ስጋታችንን አበክሬ ጠቁሜያለሁ። በሁለቱም አቅጣጫም በርከት ያለ የመዋዕለ ንዋይ ፍሰት እንደሚያስፈልግም አስረድተናል።»
ቻይና የኅብረቱ መሪዎች አዉሮጳ ለገባችበት ቀዉስ አስቸኳይ መፍትሄ እንዲያፈላልጉ ደጋግማ ስታሳስብ ቆይታለች። ከጉባኤዉ በኋላ ሁለቱ ወገኖች የንግድ ትስስራቸዉን ለማጠናከር ተፈራርመዋል።
ሸዋዬ ለገሠ
ሂሩት መለሰ