ቤኒን የወባ መከላከያ መድኃኒት
ሐሙስ፣ መስከረም 13 2008እንደዉም መድሃኒቱን ለመቀመም ጥቅም ላይ የሚዉሉት እፅዋት ከሌላ እጅ እንዳይገቡ ትልቅ ስጋት ላይ እንዳለ ነዉ የተመለከተዉ። API ቤኒን የተሰኘዉ የሕክምና መድሃኒት አምራች ኩባንያ ከ 50 በላይ ከእፅዋት የተሰሩ የሕክምና መድሃኒቶችን ያቀርባል። የመድሃኒት ኩባንያዉ የህክምና መድሃኒቶቹን የቅመማ እዉቀት ያገኘዉ ከጥንት ባህላዊ የሕክምና ዘዴ በመነሳት ነዉ። API ፓሉ የተሰኘዉ የወባ መድሃኒትም የተገኘዉ ከዚሁ ከባህላዊ የመድሃኒት ቅመማና ህክመና ዘዴ ነዉ።
« ዉጤታማና ፍቱን የሕክምና መድሃኒት ማምረት እንችላለን። ለኛ እንዲህ ያለዉን ወቅት በአፍሪቃ ብሎም ደግሞ ቤኒን ዉስጥ ማየታችን አስደሳች ነዉ። እኛ ያገኘነዉ የአፍሪቃን ችግር በአፍሪቃዉያን መፍትሄ የሚፈታ ነዉ። »
API ፓሉ የተረጋገጠ የወባ መድሐኒት ነዉ። መድሃኒቱም በአምስት የምዕራብ አፍሪቃ ሃገሮች ሥራ ላይ ዉሏል። ተመራማሪዎች ምስጋና ይድረሳቸዉ እና በዚህ የመድሃኒት ማምረቻ ኩባንያም ከ 300 በላይ የሚሆኑ ሠራተኞች መሥራት ችለዋል። ባለፈዉ የጎርጎርዮሳዊ 2014 ዓ,ም ኩባንያዉ 500 ሚሊዮን የቤንን ፍራንክን ወይም 760 ሺህ ዩሮ ገቢ አግኝቷል። ገንዘቡ ደግሞ በአካባቢዉ በጣም አስፈላጊ ለሆነዉ የመሠረተ ልማት መገንቢያ ሆኗል። በዝናባማ ወራቶች ዉስጥ በገጠር መንገዶች ላይ እንደሌሎች መኪኖች ሁሉ API ቤኒን የመድሃኒት ማመላለሻ መኪናዎች ማጥ ዉስጥ እየገቡ ተሰንቅረዉ በመቆማቸዉ ለችግር ተጋልጦ ነበር። መሠረተ ልማቱ ከተገነባ በኋላ መድሃኒቱን የጫኑ መኪኖች 100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደሚገኘዉ የኤኮኖሚ ማዕከል መሽከርከር ጀምረዋል። ይህን ከእፅዋት የተሠራ የወባ መድሐኒት ከ 25 ዓመት በፊት ለመጀመርያ ጊዜ ያገኘዉ ቤኒናዊዉ ነበር። በዚም የ API ኩባንያ ኃላፊ ቫለንቲን አጎን ለመጀመርያ ጊዜ ባገኘዉ የወባ መከላከያ ፍቱን መዳህኒቱ ይኮራል።
«በአፍሪቃ በወባ በየቀኑ 300 ሕፃናት ይሞታሉ። ይህን ያየ አንድ ተመራማሪ ለችግሩ መፍትሄ ከሌላ ቦታ ተፈልጎ እስኪ መጣ ችላ ብሎ ሊቀመጥ አይችልም። ለዚህም ነዉ ይህን በሽታ ራሳችን ለመዋጋት ቆርጠን የተነሳነዉ። እፅዋቱ ደግሞ የኛ ወላጆች እንዲሁም ቅድመ አያቶቻችንም ከዚያም በፊት ይጠቀሙበት የነበረ መድሃኒት ነዉ። »
ይህ ከባህላዊ የወባ መድኃኒት እፅ የተመረተ እንክብል የሚገኘዉ API ቤኒን የመድሃኒት መሸጫ ሱቅ ነዉ። እስካሁን ቤኒ ዉስጥ ይህ መድሃኒት የሚሽጥባቸዉ 300 ፋርማሲዎች ይገኛሉ። እንክብሉ የተሠራዉ ከእፅዋት ብቻ በመሆኑ ሌላ የሚያስከትለዉ ጉዳት እንደሌለም ቫለንቲን አጎን ይናገራል።
«እኛ የምንሸጠዉ የወባ መከላከያ መድሃኒት ዋጋ አንድ ዩሮ ከ50 ሣንቲም ነዉ። ሌላዉ አይነት የወባ መድኃኒት የሚሸጠዉ በ10 ዩሮ ነዉ። የኛ ከተፈጥሮ ከተገኘ እፅዋት የሚመረት በመሆኑ ከሌላኛዉ ይለያል። እኛ አረንጓዴ ነን ማለት ነዉ። ሌላዉ ግን ከተለያዩ ንጥረነገሮች ወይም ኬሚካሎች የሚመረት ነዉ። በአሁኑ ጊዜ ደግሞ ሰዉ የሚፈልገዉ ከእፅዋት የተሰሩ መድሃኒቶችን ብቻ ነዉ።»
የቤኒን መዲና ኮቶኑ ኗሪዎች ይህን መድሃኒት የሚገዙት በደስታ ነዉ። የወባ መድሃኒቱ ከፍቱንነቱ ሌላ ዋጋዉም ቢሆን ተመጣጣኝ በመሆኑ በዓመት 1,300 ዩሮ ገቢ ላለዉ ሕዝብ ትልቅ ትርጉም አለዉ።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ