ባንጉዊ በሤሌካ በዓማጺያን ተያዘች
እሑድ፣ መጋቢት 15 2005ማስታወቂያ
ዓማጺያኑ ከአጭር ውጊያ በኋላ የፕሬዚደንቱን ቤተ-መንግሥት ሲይዙ የአገሪቱ መሪ ፍራንሱዋስ ቢዚዜም ወደ ኮንጎ መሸሻቸው ተያይዞ ተጠቅሷል። ዓማጺያኑ ቦዚዜን ባለፈው ጥር ወር ተደርጎ የነበረ የሰላም ውልን አላከበሩም ሲሉ በመወንጀል ከሥልጣን ለማስወገድ የጥቃት ዘመቻ ሲያካሂዱ መቆየታቸው የሚታወስ ነው። የሰላሙ ውል ተኩስ-አቁምን፣ የሽግግር መንግሥት ምስረታንና በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ምርጫ መካሄዱን የሚጠቀልል ነበር። ይህ በዚህ እንዳለ ፈረንሣይ የአገሪቱን አሳሳቢ ሁኔታ በማጤን የተባበሩት መንግሥታት ጸጥታ ም/ቤት በጉዳዩ አስቸኳይ ስብሰባ እንዲያካሂድ እንደገና ጥሪ አድርጋለች። ማዕከላዊት አፍሪቃ ሬፑብሊክ ውስጥ በወቅቱ 250 የፈረንሣይ ወታደሮች ሰፍረው የሚገኙ ሲሆን የነዚህም ተግባር የአገሪቱን ዓለምአቀፍ አየር ጣቢያና 1250 ገደማ የሚጠጉ የፈረንሣይ ዜጎችን በመጠበቅ የተወሰነ ነው።
መስፍን መኮንን
ልደት አበበ