1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በጦርነቱ ጉዳት የደረሰባቸው የአፋር ክልል ጤና ተቋማት

ማክሰኞ፣ ጥር 3 2014

በሰሜን ኢትዮጵያ በጦርነት ከተጎዱት አካባቢዎች አንዱ በሆነው አፋር ክልል በርካታ የጤና ተቋማት መዘረፍ እና መውደማቸውን የአካባቢው ባለሥልጣናት እና እማኞች ይናገራሉ። የክልሉ የጤና ቢሮ ኃላፊ እንደገለጹት ወትሮም ባልጠነከረው የጤና ዘርፍ ላይ በደረሰው ጉዳት ምክንያት ከግማሽ ሚሊየን በላይ ሕዝብ ተፈላጊውን አገልግሎት ማግኘት አልቻለም።

https://p.dw.com/p/45Obv
Äthiopien Afar Zerstörung Gesundheitsbüro
ምስል Afar Health Bureau

ጤና እና አካባቢ

ኢትዮጵያ ውስጥ የጦርነትን አውዳሚነት በግላጭ መመለከት ተጀምሯል። በተለይ ገና ብዙ እንደሚቀረው አዘውትሮ በሚነገርለት የጤናው ዘርፍ ላይ የደረሰው ጉዳት ኅብረተሰቡ በያለበት መሠረታዊ የሚባሉ የጤና አገልግሎትን እንኳን እንዳያገኝ እንዳደረገው ሁኔታውን በቅርበት የሚመለከቱት ይገልጻሉ። ከዓመት የዘለለው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ተስፋፍቶ ከጎዳቸው አካባቢዎች አንዱ በሆነው አፋር ክልል የጤና ተቋማት የደረሰባቸውን ጉዳት የክልሉ የጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ያሲን ሀቢብ ለዶቼ ቬለ አብራርተዋል። የጤና ሚኒስቴር በጦርነት ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸውን በአፋር እና በአማራ ክልል የሚገኙ የጤና ተቋማት ዳግም አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ በነደፈው መርሃግብር የተለያዩ ድጋፎች እየተደረጉላቸው መሆኑ እየተነገረ ነው። በአፋር ክልልም ባለው ተመሳሳይ እንቅስቃሴ የተጎዱት የጤና ተቋማት ዳግም ወደ ሥራ እንዲመለሱ እርብርብ እየተደረገ መሆኑን የጤና ቢሮው ኃላፊ አቶ ያሲን ይናገራሉ።

Äthiopien Afar Zerstörung Gesundheitsbüro
ከጥቅም ውጪ እንዲሆኑ ከተደረጉት የጤና ተቋማት አንዱምስል Afar Health Bureau

አቶ ገአዝ አህመድ የአፋር ሰብዓዊ መብቶች ድርጅት ፕሬዝደንት ናቸው። ቤልጂየም የሚኖሩት አቶ ገአዝ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚገኙ እና በአፋርም ሆነ በአማራ ክልል ተዘዋውረው በጦርነቱ የተጎዱ ቦታቸውን መመልከታቸውን ገልጸውልናል። የመድኃኒትም ሆነ የአንዳንድ የህክምና አገልግሎት መሣሪያዎች እርዳታን በሚመለከት ከተለያዩ አካባቢዎች ወደ አፋር ክልል ሲመጡ መመልከታቸውን አቶ ገአዝ የገለጹልን ቢሆንም፤ ግን ብዙ ይቀራል ባይ ናቸው። የአፋር ክልል የጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ያሲን ሀቢብ በበኩላቸው ቃል የገቡ ወገኖች የጤና ተቋማቱን መልሶ የማቋቋሙን ሥራ ፈጠን ብለው እንዲያከናውኑ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። ሙሉ ቅንብሩን ከድምጽ ማዕቀፉ ያድምጡ።

ሸዋዬ ለገሠ

ማንተጋፍቶት ስለሺ