በኢትዮጵያ የተረጅዎች ቁጥር በ2 ሚሊዮን አሻቀበ
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 19 2009ኦሮሚያ፣የአማራና የደቡብ ብሄራዊ ክልሎች የተረጅ ቁጥር ያሻቀበባቸዉ ቦታዎች መሆናቸዉ ተገልጿል። ለተረጅወቹ ወደ 750 ሚሊዮን የሚጠጋ የአሜሪካን ዶላር ለምግብ ብቻ ያስፈልጋል ተብሏል ።
በኢትዮጵያ በተከሰተዉ ድርቅ ሳቢያ በኦሮሚያ ፣ በሶማሌና በደቡብ ብሄራዊ ክልሎች በሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች 5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሰወች ለአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ተጋልጠዉ መቆየታቸዉ ሲገለጽ ቆይቷል። በአሁኑ ወቅት ደግሞ የምግብ ርዳታ ፈላጊዉ ቁጥር ወደ 7 ነጥብ 5 ሚሊዮን ማሻቀቡን የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ገልጿል። የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ አቶ ደበበ ዘዉዴ እንደገለጹት በኦሮሚያ ፣በደቡብ ብሄርና ብሄረሰቦች እንዲሁም በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስታት የተረጅወች ቁጥር ጨምሯል።
በሀገሪቱ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ አካባቢወች የሚታየዉ አነስተኛና ስርጭቱ ያልተስተካከለ የበልግ ዝናብ ፣ በአንዳንድ አካባቢወች በተከሰተ በረዶ ፣ዉርጭ እንዲሁም ጎርፍ ሳቢያ የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ፈላጊዉ ቁጥር ሊያሻቅብ መቻሉን ሃላፊዉ አብራርተዋል።በተለይ በአማራ ክልል ይጠበቅ የነበረዉ የምርት መጠን መቀነሱን ተናግረዋል
እንደ ሐላፊዉ ገለፃ ከየካቲት እስከ ግንቦት መዝነብ የነበረበት የበልግ ዝናብ ከ 1 ወር በላይ ዘግይቷል።በዚህም ሳቢያ በቆላማዉ አካባቢ የዉሃና የመኖ እጥረት በመከሰቱ ከሰዎች በተጨማሪ በእንስሳትም ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ መሆኑ ተጠቅሷል።
ያም ሆኖ ግን በሶማሌ ክልል የተረጅወች ቁጥር አለመጨመሩን ነዉ ሃላፊዉ ነዉ የገለጹት።ከሚያዚያ ወር ጀምሮ በመንግስት በኩል ወደ አንድ መቶ አስራ አምስት ሺህ ሜትሪክ ቶን ምግብ ለተረጅዎች ማከፋፈሉም ተገልጿል።
በአሁኑ ወቅት ለተረጅወቹ ወደ 800 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ለምግብ ብቻ ያስፈልጋል ተብሏል።
ችግሩ በአየር ንብረት መዛባት ሳቢያ መከሰቱን ሃላፊዉ ገልጸዉ ከመንግስት በተጨማሪ የባለሃብቶችና የአለም አቀፍ ለጋሾች ድጋፍ ያስፈልጋል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በደረሰዉ ድርቅ ቀደም ሲል 10 ነጥብ 5 ሚሊዮን ህዝብ ለአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ተጋልጦ የነበረ ሲሆን ቆይቶ ግን ወደ 5 ነጥብ 6 መቀነሱ ተነግሮ ነበር።ባአሁኑ ጊዜ ለአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ከተጋለጡ 7 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሕዝብ ዉስጥ 3 ነጥብ 6 ሚሊዮኑ በኦሮሚያ ፣1 ነጥብ 6ሚሊዮን በሶማሌ ቀሪወቹ በአማራና በደቡብ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስታት የሚገኙ መሆኑን ኮሚሽኑ ገልጿል።
ፀሐይ ጫኔ
ነጋሽ መሀመድ