በአፍሪቃ ቀውስና መፃኢ ዕድሎች
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 14 2007በምዕራብ አፍሪቃ የተቀሰቀሰው የኢቦላ ወረርሺኝ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ሕይወት ከመቅጠፉም ባሻገር የሃገራቱን ምጣኔ ሀብት በከፍተኛ ደረጃ እንደጎዳው እየተነገረ ነው። የተመድ ዋና ጸሓፊ ባን ኪሙን የኢቦላ ወረርሺኝ በቅርቡ በቁጥጥር ስር ሊውል ይችላል የሚል ተስፋ እንዳላቸው ተጠንቅቀው ተናግረዋል። የጀርመን መራሒተ-መንግሥት የአፍሪቃ ልዕክ ጉይንተር ኑክ የዋና ጸሓፊውን ሀሳብ ይጋራሉ።
«ቀደም ሲል ከታየው የበለጠ ስኬት እናስመዘግባለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። የተሐዋሲው የመሰራጨት ፍጥነት እጅግ በጣም ቀንሷል።»
በእርግጥ ግን የኢቦላ ተሕዋሲ ስርጭትን ሙሉ ለሙሉ ለመቆጣጠር ኅብረተሰቡን ሰፋ ያለ ግንዛቤ ማስጨበጥ እንደሚያሻ የአፍሪቃ ልዑኩ አስገንዝበዋል። ተሐዋሲው በምዕራብ አፍሪቃ ሦስት ሃገራት ማለትም ላይቤሪያ፣ ሴራሊዮን እና ጊኒ ከፍተኛ የምጣኔ ሀብት ጉዳት ማስከተሉም ተገልጧል። በተለይ በሴራሊዮን በርካታ የንግድ ድርጅቶች ለመዘጋት መገደዳቸውን ጉይንተር ኑክ ተናግረዋል። ምዕራብ አፍሪቃ ላይ የታየው መጠነኛ የምጣኔ ሀብት እድገትም አደጋ እንደተጋረጠበት ልዑኩ አስገንዝበዋል።
«በእርግጥም መጠነኛ የምጣኔ ሀብት እድገቱን ሠንጎ የያዘ አዲስ ሳንካ ተጋርጧል። ወረርሽኙ የፈጠረውን ቀውስ ተከትሎ ሃገራቱ መገለል ስለደረሰባቸው በከፍተኛ ደረጃ ተጎድተዋል። እንደ አዲስ ከታች መጀመር ሊኖርባቸው ነው። በዛ ላይ በምዕራብ አፍሪቃ የረሀብ አደጋ ማንዣበቡ ተረጋግጧል።»
ይኽ የረሀብ አደጋ ከምዕራብ አፍሪቃ ባሻገርም በደቡብ ሱዳን ማንዣበቡን ልዑኩ ይፋ አድርገዋል። የደቡብ ሱዳን መንግሥት እና አማፂያን በሚያኪያሄዱት ጦርነትነት የተነሳ የረሀብ አደጋው መጋረጡ በተደጋጋሚ ተጠቅሷል። ከአፍሪቃ ጋር በሚደረገው የንግድ እንቅስቃሴ ፍትኃዊ ንግድ ወሳኝ መሆኑን ልዑኩ አበክረው ተናግረዋል።
«ወሳኙ ነገር ገበያው ክፍት ሲደረግ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው የነፃ ገበያው ሳይሆን ፍትኃዊ ግብይት ማከናወኑ ነው። ግብይቱ የሠብዓዊ መብቶችን በተመለከተ ያስቀመጥነውን መስፈርት የሚገነዘብ መሆን አለበት።»
የጀርመን መንግስት የምዕራብ አፍሪቃ ሃገራት የኢቦላ ተሐዋሲ ካደረሰባቸው ጥፋት ለማገገም በሚያደርጉት ጥረት ትብብሩ እንደሚቀጥልጉይንተር ኑክ አስታውቀዋል።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሰ