1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በአውሮፕላን አደጋ ለሞቱ የሐዘን ሥነ-ሥርዓት ተካሔደ

እሑድ፣ መጋቢት 8 2011

የኢትዮጵያ አውሮፕላን ተከስክሶ ሕይወታቸውን ላጡ የሐዘን ሥነ-ሥርዓት ተካሔደ። መርሐ ግብሩ በአዲስ አበባ ቅድስት ስላሴ ካቴድራል እና በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተካሒዷል። የሟች ቤተሰቦች፤ የሐይማኖት መሪዎች፣ ባለስልጣናት እና በርካታ ኢትዮጵያውያን ሐዘናቸውን ለመግለጽ በቦታዎቹ ተገኝተዋል።

https://p.dw.com/p/3FDCo
Äthiopien Trauerfeier Flugzeugabsturz Boeing 737 Max
ምስል picture-alliance/AP Photo/M. Ayene

ከሳምንት በፊት ከቢሾፍቱ አቅራቢያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን በመከስከሱ ሕይወታቸውን ያጡ መንገደኞች የሐዘን ሥነ-ሥርዓት አዲስ አበባ በሚገኘው ቅድስት ስላሴ ካቴድራል ተካሔደ። በሥነ-ሥርዓቱ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ የለበሱ 17 ባዶ የሬሳ ሳጥኖች በመታሰቢያነት ቀርበዋል። በመርሐ ግብሩ የሟች ቤተሰቦች በከፍተኛ ሐዘን ተውጠው ታይተዋል። የሐዘን ሥነ-ሥርዓቱ የተካሔደው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለሟች ቤተሰቦች ለ157ቱ መንገደኞች ቤተሰቦች አፈር መስጠት ከጀመረ ከአንድ ቀን በኋላ ነው። አየር መንገዱ አውሮፕላኑ ከወደቀበት ቦታ በከረጢት የታሸገ አንድ ኪሎ አፈር ለመስጠት የተገደደው የሟቾቹን ማንነት የመለየቱ ሥራ ረዥም ጊዜ ስለሚወስድ ነው።

በቅድስት ስላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን በተከናወነው የሐዘን ሥነ-ሥርዓት የሟቾች ቤተሰቦች፣ የስራ ባልደረቦች፣  ወዳጅ ዘመዶቻቸው በብዛት ተገኝተው እርማቸውን አውጥተዋል።  የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኞች እና አመራሮች በአደጋው ሕይወታቸውን ያጡ ባልደረቦቻቸውን ለማሰብ በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተመሳሳይ የሐዘን ሥነ-ሥርዓት አካሒደዋል።  

Äthiopien Trauerfeier Flugzeugabsturz Boeing 737 Max
ምስል picture-alliance/AP Photo/M. Ayene

የመንገደኞች ቤተሰቦች ካናዳን ከመሳሰሉ አገሮች ወደ ኢትዮጵያ በመጓዝ ላይ ናቸው። የፈረንሳይ የበረራ ደኅንነት ምርመራ ባለሥልጣን በትናንትናው ዕለት ከተከሰከሰው አውሮፕላን የመረጃ ማጠራቀሚያ ሳጥን አስፈላጊ ሰነዶች በተሳካ መንገድ ማውጣታቸውን አስታውቀዋል።

Äthiopien Trauerfeier Flugzeugabsturz Boeing 737 Max
ምስል Getty Images/J. Countess

ባለሥልጣኑ መረጃው ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለሥልጣናት ማስረከቡን አስታውቋል። በተለምዶ ጥቁር ሳጥን (ብላክ ቦክስ) ተብሎ በሚጠራው የመረጃ ማጠራቀሚያ ሳጥን የሚገኙ የድምፅ ሰነዶች በፈረንሳይ የበረራ ደኅንነት ምርመራ ባለሥልጣን አለመደመጣቸውም ተገልጿል። 

እሸቴ በቀለ