በአማራ ክልል የተወሰኑ አካባቢዎች የጦር መሳሪያ ይዞ መንቀሳቀስ ተከለከለ
እሑድ፣ የካቲት 10 2011የአማራ ክልል የሰላም ግንባታ እና የሕዝብ ደኅንነት ጉዳዮች ጽ/ቤት ኃላፊ ብርጋዴየር ጄነራል አሳምነው ጽጌ ለDW እንደተናገሩት የጦር መሳሪያ ክልከላ «ውሳኔው የተላለፈው የኅብረተሰቡን ጤንነት እና ደኅነት ከመጠበቅ አንጻር ነው።» ኃላፊው ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በጎንደር መተማ መስመር ላይ ይስተዋላሉ ያሉ ወንጀሎችን ዘርዝረዋል።
«ይሄ መስመር ሕገ ወጥ የሆኑ ሰዎች በተለያየ መንገድ የተደራጁ ሰዎች መኪና እያስቆሙ የሚገሉበት፣ የሚዘርፉበት፣ ማጅራት የሚመቱበት የተለያየ ወንጀል የሚፈጽመበት ነው። መኪናዎች በጥይት ይመታሉ፣ ሰዎች ይታፈናሉ፣ ዘልለው በዚያ ቀጠና ውስጥ ይገባሉ። ስለዚህ የዜጎች ሕይወት በዚያ ቀጠና ውስጥ አደገኛ ሁኔታ ውስጥ ወድቋል ማለት ነው። ስለዚህ ከዚህ በመነሳት ይህን ዓለም አቀፍ መስመር ለተጠቃሚዎችም ወይም ደግሞ ለተፈላጊው ዓላማ ክፍት ማድረግ አለብን። የመንግስት አንዱ ኃላፊነት እና ግዳጅም ይኼ ነው። ስለዚህ እነዚህ ጥፋተኞች በዚያ እና በዚህ በመንገዱ እየተጠቀሙበት ስላለ አንደኛ መንገዱን አደጋን የማያስከትል ማድረግ ነው፣ ሁለተኛ እዚያ አካባቢ ጥቃት እንዳይደርስ እና እንዲህ አይነት ግለሰቦች ደግሞ ታጥቀው ከተገኙ ደግሞ ለዚያ ዓላማ መሆኑ ታውቆ መንግስት አስፈላጊውን ክትትል አድርጎ እርምጃ ይወስዳል» ሲሉ ለDW ገልጸዋል።
«ተመሳሳይ እና ተያያዥ ችግሮች» ከጎንደር በድንጋይ ትክል እስከ ሁመራ ድረስ ባለው መስመርም እንደሚስተዋል የተናገሩት ብርጋዴየር ጄነራል አሳምነው በዚያ መንገድም በአምስት ኪሎ ሜትር ክልል የጦር መሣሪያ ይዞ መንቀሳቀስ ተከልክሏል ብለዋል። «ወንጀል ፈጽመው ጎንደርን ከተማን እንደ መደበቂያ፣ እንደ ምሽግ የሚጠቀሙ ኃይሎች አሉ ያሉት» ኃላፊው ይህን ለመከላከል በከተማይቱ ከሕጋዊ እና የመንግሥት ታጣቂዎች ውጪ የጦር መሣሪያ ታጥቆ መንቀሳቀስ እንደተከለከለ አስረድተዋል። ሆኖም በከተማይቱም ሆነ በአውራ ጎዳናዎቹ ላይ የሰዓት እላፊ አልታወጀም ብለዋል።
ዛሬ ይፋ የተደረገው ክልከላ ከሳምንታት እስከ ወር ሊቆይ እንደሚችል የገለጹት ብርጋዴየር ጄነራል አሳምነው ሆኖም በረጅም ጊዜ ለውጥ ካልመጣ የክልሉ አመራር ለሁኔታው የሚመጥን ውሳኔ ወደፊት እንደሚወስን አብራርተዋል። ክልከላውን ጥሶ በተገኘ ማንኛውም ግለሰብ ወይም ቡድን ላይ በጸጥታ ኃይሎች የሚወሰደው እርምጃም «ሕግን የተከተለ» ይሆናል ብለዋል።
ከብርጋዴየር ጄነራል አሳምነው ጽጌ ጋር የተደረገውን አጠር ያለ ቃለ ምልልስ ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።
ተስፋለም ወልደየስ
ማንተጋፍቶት ስለሺ