በናይጄሪያ የኒጄር ዴልታ ኣካባቢ ብክለትና ውዝግቡ
ዓርብ፣ ጥቅምት 29 2006በአካባቢው የነዳጅ ምርት ላይ ተሰማርቶ የሚገኘው የሼል ኩባኒያ በበኩሌ የነዳጅ መተላለፊያ መስመሮቹ የፈነዱት የአካባቢው ኗሪዎች ባስከተሉት ችግር ሲል ይከራከራል።
ዓለም ዓቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አመነስቲ ኢንተርናሺናል ትላንት ባወጣው ሪፖርቱ የናይጄሪያን መንግስት ወቅሷል።
በናይጄሪያ በነዳጅ ዘይት ምርት በምትታወቀው የኒጀር ዴልታ ክ/ሀገር ከድፍድፍ ነዳጅ ማስተላለፊያዎች ነዳጅ ወደ አካባቢ የማፈትለኩ ዜና የተሰማው የዛሬ 8 ዓመት ገደማ ነበር እ ኣ ዘ ኣ በ 2005 ዓ ም። ፍሰቱም እስከ ዛሬ በዓለም ላይ ከታዩት ከፍተኛ የነዳጅ ዘይት ፍሰቶች ኣንዱ ነው ተብሏል። በዚያ ላይ የአካባቢ ብክለቱን ለማከምም ሆነ የብክለቱ ሰለባ ለሆኑ የአካባቢው ኗሪዎች የጉዳት ካሳ ባለመከፈሉ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ችግሩን ኣስከፊ ኣድርጎታል።
ይህንን ከመሰለው ብክለት ጋር መኖሩ ደግሞ ምን ያህል ኣስቸጋሪ እንደሆነ ከገመገሙት መካከል ሳም ኣሉኮያ እንደሚለው በባይልሳ ግዛት ኦሩማ መንደር የህጻናት መዋኛ ውኃ ተበክሎ ካለፉት 8 ዓመታት ወዲህ ልጆች የተለመደ መዝናኛቸውን ጤናማ በሆነ መልኩ ሊጠቀሙበት ኣልቻሉም።
ብክለቱ እጅግ በጣም መጠነ ሰፊ ከመሆኑ የተነሳ ኣንዳንድ ገበሬዎችም ከዚያ ወዲህ ወደ ማሳቸው ተመልሰው ለማረስ ኣለመቻላቸውን ይናገራሉ። ኣርሶ ኣደር ኢኑኬ ቢላኪ ከሰለባዎቹ ኣንዱ ነው።
« ከ 2005 ዓ ም ጀምሮ ይህ ብክለት እርሻዬን ከጥቅም ውጪ ኣድርጎታል። ነዳጅ ዘይቱ ኣሁንም በእርሻዬ ውስጥ ነው የሚተለለፈው። ከዚያ ወዲህ ማሳዬን ማረስ ኣልቻልኩም። እንደምታዩት ይኸው ኣሁንም ድረስ መሬቱ የሚሆን ኣይደለም። ሼል ወደዚህ አካባቢ የመጣው ሁለመናውን ለመበከል ነው። ብክለቱ ላደረሰብን ጉዳትም ኣንዳች ነገር ካሳ ኣልከፈልንም።»
በሌላኛው መንደር በዓሳ ማስገር ስራ ለይ ተሰማርቶ ይኖር የነበረው ኣላሴ ኢፋጋም እንዲሁ ዓሳ የሚያሰግርበት ኩሬ ተበክሎ ኣሁንም ድረስ ከአገልግሎት ውጪ መሆኑን እና ለደረሰበት ጉዳት ደግሞ የሼል ኩባኒያ ካሳ ለመክፈል ፈቃደኛ ኣለመሆኑን ነው በምሬት የሚናገረው።
«ሼል ,,,,የነዳጅ ፍሰቱ በደረሰበት ወቅት እኔ ከዚያ ሌላ ምንም ነገር ኣልነበረኝም። ምክኒያቱም ያ ለኔ የመጨረሻ ተስፋ ነው የነበረው። በዚህ ጉዳይ ከሼል ጋር ለመነጋገር ያላደረግሁት ጥረት የለም። ኣልተሳካም። እነሱ ምንም ነገር ለመቀበል ኣይፈቅዱም።ኃላፊነትም መውሰድ ኣይፈልጉም።»
የሼል ኩባኒያም ሆነ በኒጀር ዴልታ የነዳጅ ምርት ስራ ላይ የተሰማሩት ሌሎች የምዕራባዊያን ኩባኒያዎችም በዚህ ጉዳይ ላይ ከኃላፊነት ለመሸሽ የተስማሙ ይመስላሉ። ሁሉም ቢሆኑ ቱቦዎቹ የፈነዱት የአካባቢው ሰዎች በተንኮል ገንዘብ ለማስከፈል ወይንም ለስርቆሽ ከመስመሮቹ ጋር በሚታገሉበት ወቅት ነው ይላሉ።
ይሁንና የ ተ መ ድ ጨምሮ በሌሎች ገለልተኛ የሆኑ አካላት የተካሄዱ ምርመራዎች እንደሚያመለክቱት በነዳጅ ዘይት ፍሰት ለተበከለው የኒጀር ዴልታ አካባቢ የነዳጅ ዘይት ኩባኒያዎች ተጠያቂ ናቸው። ጥያቄው ማን ይጠይቃቿል? የሚለው ሲሆን ምክኒያቱ ደግሞ በምርመራዎቹ መሰረት ከማጣራት ኣንስቶ ተጠያቂ እስከማድረግ ድረስ ኃላፊነት ያለባቸው የመንግስት ተቐማት ከእነዚህ ኩባኒያዎች ጋር እጅና ጉዋንት በመሆናቸው ጉዳዩን እጅግ ውስብስብና ኣስቸጋሪ ኣድርጎታል።
ዓለም ዓቀፉ የሰብዓዊ መብት ተፋላሚ ድርጅት አመነስቲ ኢንተርናሺናልም በትላንትናው ዕለት የችግሩን ውስብስብነት ጠቅሶ ዘግቧል። ለሰለባዎቹ ካሳ ካለመከፈሉ ጋር ብክለቱ በአካባቢው ህብረተሰብ ላይ ያስከተለው ጉዳት በቀላሉ የሚገመት ኣይደለም ያለው አመነስቲ ኢንተርናሺናል የናይጄሪያንም መንግስት ወቅሷል። ሌሎች የአካባቢው ኣገሮችም በነዳጅ ዘይት ኩባኒያዎች ላይ የሚያደርጉትን ቁጥጥር ያጠናክሩ ዘንድ ኣሳስቧል።
የሼል ናይጄሪያ ኃላፊዎች በበኩላቸው አመነስቲ ኢንተርናሺናል ስለምን እንደሚያወራም ኣልገባንም ሲሉ ዘገባውን ኣጣጥለውታል።
ሌላው የሼል ኩባኒያ ኣሻጥር አመነስቲ ኢንተርናሺናል እንደሚለው ወደ ኣካባቢ የፈሰሰውን ድፍድፍ ነዳጅ መጠን ኣሳንሶ ማቅረብ ሲሆን ሼል እስከ ኣሁን ያመነው 1640 በርሜል ያህል ነው። ኣመነስቲ ኢኒተርናሺናል መረጃዎችን ጠቅሶ እንደዘገበው ግን በኒጀር ዴልታ ወደ ኣካባቢ የፈሰሰው ድፍድፍ ዘይት መጠን ሼል ካመነው 60 ጊዜ እጥፍ ነው።
ጃፈር ዓሊ
ሸዋዪ ለገሰ