በምሥራቃዊ ኮንጎ የቀጠለው ውጊያ
ቅዳሜ፣ ሰኔ 2 2004እንዲያቋርጡ ጉዳዩ ያሳሰበው ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጠይቋል።
መጋቢት ሀያ ሦስት » በመባል የሚታወቀውና ሕፃናትን ለውጊያ ተግባር መልምለዋል በሚል ክስ በዓለም አቀፉ የጦር ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት የሚፈለጉት ቦስኮ ንታንጋንዳ የመሩት፡ በኮንጎ ይንቀሳቀስ የነበረው፡ በምሕፃሩ CNDP የተባለው ብሔራዊው የሕዝብ መከላከያ ኮንግረስ ቡድን አባላት የሆኑት የቱትሲ ዓማፅያን መጋቢት 2009 ዓም በተደረሰ የሰላም ስምምነት አማካኝነት የኮንጎን ጦር የተቀላቀሉ ሲሆኑ፡ በጦር ኃይሉ ውስጥ ጥሩ አያያዝ አልተደረገልንም በሚል ነው ያመፁት። ውጊያው በሰሜን እና በደቡብ ኪቩ አካባቢ ከተጀመረ ወዲህ፡ ቢያንስ ሁለት መቶ ዓማፅያን እና ወደ አርባ የሚጠጉ የመንግሥቱ ወታደሮች መገደላቸውን የኮንጎ መንግሥት ጦር ያወጣው አንድ ዘገባ አመልክቶዋል። ወደ ሀያ ሺህ የሚጠጋ ሰውም ውጊያውን ለመሸሽ ሲል አካባቢውን ለቆ ወደ ጎረቤት ርዋንዳ እና ዩጋንዳ ተሰዶዋል። የኮንጎ መንግሥት አንድ የተዋኃደ ጦር ኃይል መፍጠር በሀገሩ የመረጋጋት ሁኔታን ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን በማመን በጦር ኃይሉ ውስጥ አለ በሚል የሚቀርበው የሰብዓዊ መብት ረገጣን ለማስወገድ ጥረት መጀመሩን አስታውቋል።
ስለኮንጎ ጊዚያዊ ሁኔታ፡ በሰሜንና ደቡብ ኺቩ አካባቢ በመንግሥቱ ጦርና ከጦሩ በከዱ ዓማፅያን መካከል እንዳዲስ ስላገረሸው ውጊያ፡ እንዲሁም፡ ርዋንዳ እነዚህን ዓማፅያን ትርኣለች ስለመባሉ የጀርመናውያኑ የፍሪድሪኽ ኤበር ተቋም ሰሞኑን አንድ ጉባዔ አካሂዶ ነበር። በውይይቱ ከተሳተፉት መካከል አንዱ የሆኑት የኮንጎ ክርስቶስ ቤተክርስትያን ቄስ ዣን ሙቶምቦ በኪቩ አካባቢ ውጊያው እንደገና ለተነሳበት ድርጊት በዚያ ያለው የተፈጥሮ ሀብት ንጣፍ ምክንያት ነው ይላሉ።
«ውጊያው ለምን ይሆን በምሥራቁ የሀገሪቱ አካባቢ ብቻ እንደገና የተጀመረው? በግጭቱ እንደገና ማገርሸት እና ባካባቢው ያለውን የተፈጥሮ ሀብት በመበዝበዙ መካከል ግንኙነት እንዳለ በግልጽ እናውቃለን። ብዙዎቹ የጦር ኃይሉ ኃላፊዎች እና የመንግሥ ሠራተኞች የተፈጥሮ ሀብቱ የሚወጣባቸውን አካባቢዎች በመቆጣጠራቸው የሀገሪቱ መንግሥት ሥልጣኑን በዚህ አካባቢ እንዲጠናከር አይፈልጉም። እና እኔ እንደሚመስለኝ በዚሁ አካባቢ ያለው የተፈጥሮ ሀብት መዳብ ወይም የዛፍ ግንድ ቢሆን ኖር ጦርነት አይነሳም ነበር፤ ግን እዚህ ያለው ኮልታን የተባለው ማዕድን ነው። »
ማዕድኑ ኮልታን ደግሞ የእጅ ስልክ እና ተንቀሳቃሹን ኮምፒውተር ለማምረት አስፈላጊ ነው።
በሰሜን እና በደቡብ ኪቩ በተለይ በቡናጋናና በማሲሲ አካባቢ ውጊያው እንደገና ለተጠናከረበት ድርጊት ተጠያቂው ቦስኮ ንታንጋንዳ መሆናቸውን የሰሜን ኪቩ አስተዳዳሪ ጁልየን ፓሉኩ በርግጠኝነት ተናግረዋል።
« በዚሁ በማሲሲ አካባቢ በወቅቱ እየታየ ላለው ሁኔታ በኃላፊነት የሚጠየቁት ቦስኮ ንታንጋንዳ ናቸው ብለን በወቅቱ መናገር እንችላለን። በመንግሥት ቁጥጥር ሥር በሚውሉበት ጊዜ ለተግባራቸው ኃላፊነት መውሰድ ይኖርባቸዋል። »
ንታንጋንዳ ተጠያቂ ናቸው የሚሉት ለአፍሪቃውያን የሰብዓዊ መብት የሚሟገተው ህብረት ፕሬዚደንት ዦን ክሎድ ካቴንዴም ንታንጋንዳ ታስረው ለፍርድ መቅረብ አለባቸው ነው የሚሉት።
« በዚሁ አካባቢ ለሚታየው ሁኔታ ቦስኮ ንታጋንዳ ተጠያቂ ናቸው፤ እሳቸውን ማሰር ጥሩ ነገር ነው ብለን እናስባለን ምክንያቱም መንግሥት ንታጋንዳን አስሮ አንድም በብሔራዊው ፍርድ ቤት ወይም ጉዳያቸውን በመመርመር ላይ ባለው በኮንጎ የሰላም አፈላላጊ ቡድን ፊት ለፍርድ ለማቅረብ ጥረት ከጀመረ ብዙ ዓመታት ሆነዋል። በሰላም ስም ለወንጀለኞች ከለላ መስጠት ልንቀጥል አንችልም። የታወቁ ወንጀለኞችን በማሰር ጥሩ አርአያ ካልሆንን በስተቀርን፡ ሌሎችም ቅጣት አይደርስብንም በሚል ሊከተሉ ይችላሉ። »
በዦን ክሎድ ካቴንዴ አስተሳሰብ፡ ንታጋንዳን የመሳሰሉ ወንጀለኞች እንዲታሰሩ ዴሞክራቲክ የኮንጎ ሬፓብሊክን ለማረጋጋት በሀገሪቱ የተሰማራው የተመድ ሰላም አስከባሪ ሠራዊት፡ በምህፃሩ ሞኑስክ የበኩሉን ድርሻ ማበርከት ይጠበቅበታል። የርዋንዳ ዜጎች የኮንጎ «መጋቢት ሀያ ሦስት » ዓማፅያንን እንዲረዱ መሠልጠናቸውን ሞኑስክ ባወጣው ዘገባ አረጋግጦዋል። በኮንጎ የሰላም አስከባሪው ተልዕኮ ኃላፊ ሮዤ ሜስ እንዳስታወቁት፡ ሞኑስክ ዘገባውን ያጠናቀረው ከዓማፅያኑ ቡድን ከከዱ አሥራ አንድ የርዋንዳ ዜጎች ከሆኑ ተዋጊዎች ጋ ጭምር ባደረገው ቃለ ምልልስ ነው። በዘገባው መሠረት፡ ርዋንዳውያኑ ሙንዴዴ በተባለ የርዋንዳ መንደር ከሠለጠኑ በኋላ ወደ ዴሞክራቲክ የኮንጎ ሬፓብሊክ ተልከዋል።
« እኛ የሞኑስክ አባላት ርዋንዳ ውስጥ የሚደረገውን ነገር ሄደን የማጣራት አቅሙ የለንም። ይህ ኪንሻሳ እና ኪጋሊ በጋራ ባቋቋሙት ዘዴ የተጣራ ጉዳይ ነው። በሁለቱ መንግሥታት ከ 2009 ዓም ወዲህ በተሻሻለው ግንኙነታቸው አማካኝነት ለዚህ ጉዳይ መፍትሔ እንደሚያገኙለት ተስፋ አደርጋለሁ። በወቅቱ የሚታየውን ግጭት ማብቃቱ በጣም አስፈላጊ ነው። ኮንጎ ብቻ ሳትሆን ሌሎች ያካባቢው ሀገሮችም ባካባቢው መረጋጋት እና ሰላም እንዲኖር ይፈልጋሉ። በምሥራቅ ኮንጎ ፡ በርዋንዳ ወይም በቡሩንዲ ወይም በሌሎች ያካባቢ ሀገሮች መረጋጋት ሳይኖር ባካባቢው ዘላቂ ሰላም በፍፁም አይኖርም። »
ልክ እንደ ሞኑስክ፡ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ቡድን ሂውመን ራይትስ ዎችም ከጥቂት ጊዜ በፊት ያወጣው ዘገባ እንዳመለከተው፡ በብዛት የቱትሲ ጎሣ አባላት የሚጠቃለሉበት የርዋንዳ መንግሥት በእሥራት የሚፈለጉት ቦስኮ ንታጋንዳ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ባለው ድንበር አካባቢ እና በርዋንዳም በነፃ እንዲዘዋወሩ ከመርዳቱ ጎን፡ «ለመጋቢት ሀያ ሦስት » ዓማፅያን የሚሊሺያና የጦር መሣሪያ ድጋፍም ሰጥቷል። በኪጋሊ የሚገኘው የርዋንዳ መንግሥት ግን የተመድን እና የሂውመን ራይትስ ዎች ወቀሳን ሀሰት ሲል አስተባብሎዋል።
እአአ የፊታችን ሰኔ ሠላሣ የሚያበቃውን የኮንጎ የተመድ ሰላም አስከባሪው ተልዕኮን እንዲያራዝም የተመድ ፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤትን ለማግባባት የሞኑስክ፡ ኃላፊ ሮዤ ሜስ የበርሊኑ የፍሪድሪኽ ኤበርት ተቋም ጉባዔ እንዳበቃ ወደ ኒው ዮርክ ተጉዘዋል።
አርያም ተክሌ
መስፍን መኮንን