1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሻሸመኔ ከድምፃዊ ሐጫሉ ሁንዴሳ ግድያ በኋላ

ሐሙስ፣ ሐምሌ 9 2012

ከሐጫሉ ሞት በኋላ በተቀሰቀሱ ግጭቶች እና የጸጥታ አስከባሪዎች በወሰዷቸው እርምጃዎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል። ከዚያ ባሻገር እንደ ሻሸመኔ ባሉ ከተሞች በርካታ ንብረት ወድሟል። በሻሸመኔ በመቶዎች የሚቆጠሩ መኖሪያ ቤቶች፣ ሆቴሎች እና የተለያዩ መደብሮች ለተቃውሞ በወጡ ቡድኖች ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል።

https://p.dw.com/p/3fPey

አቶ ግርማ ከአስር አመታት በፊት በሻሸመኔ ከተማ የመሠረቱት ትምህርት ቤት ከሐጫሉ ሁንዴሳ ግድያ በኋላ ለተቃውሞ አደባባይ በወጡ ሰዎች ሲቃጠል ከሩቅ ሆኖ ከመመልከት የዘለለ ምርጫ አልነበራቸውም።

ዕድሜ ልካቸውን በፍጥነት በማደግ ላይ በምትገኘው በሻሸመኔ ከተማ ቢኖሩም ኦሮሞ ባለመሆናቸው ብዙ ጊዜ እንደመጤ ይቆጠራሉ። ትምህርት ቤታቸው ሲቃጠል ለማዳን ሙከራ ቢያደርጉ ኖሮ ሕይወታቸውን ሊያጡ ይችሉ እንደነበር ያስባሉ። "የፈለጉትን ነገር እንዲያደርጉ ከፈቀድክላቸው አይነኩህም። ንብረትህን ለመታደግ ከፈለክ፤ ጥረት ካደረክ ግን ወደ አንተ ይመጣሉ" ይላሉ ለደሕንነታቸው በመስጋት ማንነታቸው እንዳይታወቅ ሙሉ ስማቸውን ከመናገር የተቆጠቡት አቶ ግርማ።

የአቶ ግርማን ንብረት ለውድመት የዳረገው ተቃውሞ የተቀሰቀሰው ባለፈው ሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. የድምፃዊ ሐጫሉ ሁንዴሳ መገደል ነበር።

ከሐጫሉ ሞት በኋላ በተቀሰቀሱ ግጭቶች እና የጸጥታ አስከባሪዎች በወሰዷቸው እርምጃዎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል። ከዚያ ባሻገር እንደ ሻሸመኔ ባሉ ከተሞች በርካታ ንብረት ወድሟል።

በሻሸመኔ በመቶዎች የሚቆጠሩ መኖሪያ ቤቶች፣ ሆቴሎች እና የተለያዩ መደብሮች ለተቃውሞ በወጡ ቡድኖች ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል። በተለይ ኦሮሞ ያልሆኑ ሰዎች ንብረቶች የጥቃቶቹ ዒላማ ሆነዋል።

"የወደመው ንብረት ከዚህ በፊት በነበሩ አለመረጋጋቶች ከታየው ሁሉ የከፋ መሆኑን እስካሁን ያከናወንው ጥናት ይጠቁማል" ሲሉ የሒውማን ራይትስ ዎች የአፍሪካ ቀንድ ቢሮ ዳይሬክተር ላቲታ ባድር ለፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ተናግረዋል።

ኦሮሞ ላልሆኑ የጥቃቱ ሰለባዎች ለረዥም ጊዜ ቤቴ ብለው ይጠሩት በነበረው አካባቢ ከዚህ በኋላ ቦታ እንደማይኖራቸው የሚጠቁም ነው። በሻሸመኔ የነበራቸው ሆቴል የወደመባቸው አልማዝ ሞርጋን ቻፕማን "ቁልፍ ቦታዎችን መርጠው በማቃጠል በተከተሉት ስልት ምክንያት ሰዎች ተመልሰው እንዲመጡ የፈለጉ አይመስለኝም" ብለዋል።

የኦሮሞ ሕይወት ዋጋ አለው

የሻሸመኔ ከተማ በራስ ተፈሪያን መቀመጫነቷ ትታወቃለች። ከተማዋ በምሥራቅ አፍሪካ ስምጥ ሸለቆ ዋንኛ የንግድ ማዕከል ከሆኑት መካከልም አንዷ ነች። ይኸ ለጥቃት ሰለባ የሚሆኑ በርካታ ንብረቶች የሚገኙባት ከተማ ያደርጋታል። በከተማዋ ዋና መንገድ የንግድ መደብሮች ተዘርፈው በእሳት መጋየታቸውን፣ መስኮቶቻቸው መሰባበራቸውን በመስመር የቆሙ ተሽከርካሪዎች መቃጠላቸውን የእግረኛ መንገዶችም በውድቅዳቂ ብረቶች መሞላታቸውን የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።

በከተማው ከተዘረፉ የመድን ዋስትና ሰጪ ኩባንያ ሕንፃዎች በአንዱ የኦሮሞ ሕይወት ዋጋ አለው  (OROMO LIVES MATTER) የሚል ጽሁፍ እንደሚገኝ ይኸው ዘገባ ይጠቁማል። የዛኑ ያክል ጥቃት ያልተፈጸመባቸው ትምህርት ቤቶች እና ምግብ ቤቶች ይገኛሉ። አብዛኞቹ የኦሮሞዎች ንብረት እንደሆኑ የከተማዋ ነዋሪዎች ለፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ተናግረዋል።

አልማዝ ሞርጋን ቻፕማን ከትሪንዳድ እና ቶቤጎ ወደ ሻሸመኔ አቅንተው ከ15 አመታት በፊት የከፈቱት 28 የመኝታ ክፍሎች የነበሩት ሆቴል የሐጫሉ ሁንዴሳ ግድያ በተሰማ በሰዓታት ልዩነት በተቃዋሚዎች በእሳት ጋይቷል። እርሳቸውም የለሊት ልብሳቸውን ብቻ እንደለበሱ ቅጥር ግቢውን ጥለው ሸሽተዋል። አሁንም ኢትዮጵያን እወዳለሁ ያሉት አልማዝ ሞርጋን ቻፕማን "ሥራዬን በመቀጠል ረገድ ግን በኩል እኔ ግን ጨርሻለሁ፤ ጡረታ ወጥቺያለሁ" ሲሉ ለፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ተናግረዋል።