ሶስት ረመዳን በመጠለያ፤ ሶስት ኢድ በመጠለያ
እሑድ፣ ግንቦት 16 2012ማስታወቂያ
ጠቅላይ ምኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሥልጣን በያዙ ማግስት በተለያዩ አካባቢዎች በተከሰተው ግጭት ተፈናቅለው ድሬደዋ የተጠለሉ ከአራት ሺህ በላይ ዜገች ሶስት አመታትን በመጠለያ ማሳለፍ ግድ ሆኖባቸዋል። ለሶስተኛ ጊዜ የረመዳን የፀም ወቅትን በመጠለያው ማሳለፋቸውን የሚናገረው የመጠለያው አስተባባሪ አቶ ቦቆሬ ሀሰን በተለይ ዛሬ የተጠናቀቀው የረመዳን ወቅት ከባድ እንደነበር ገልጿል።
«ከዛሬ ነገ ከመጠለያ ወጥተን ወደ መደበኛ ህይወት እንሸጋገራለን» በሚል ተስፋ ሶስት አመታትን በመጠለያው ያስቆጠሩት እነዚህ ተፈናቃዮች ከአንድ ሺህ በላይ ህፃናቶቻቸው ትምህረት እየተማሩ አለመሆናቸውንም አቶ ቦቆሬ ተናግረዋል።
«በቅርብ ጊዜ መፍትሄ ታገኛላችሁ» ከሚል የዘለለ ዛሬም የተጨበጠ ነገር አለመኖሩን የሚናገረው አቶ ቦቆሬ በቅርቡ መፍትሄ ይደረጋል መባሉን እንደሰማ ተናግሯል፡፡
የድሬደዋ አደጋ ስጋት ቅነሳ ማስተባበርያ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሀርቢ ቡህ ለእነዚህ ዜጎች ዘላቂ መፍትሄ የመስጠት ሓላፊነት የሶማሌ ክልል መሆኑን ጠቅሰው በቅርቡ ከክልሉ ሃላፊዎች ጋር በተካሄደ ውይይት ከረመዳን ፆሙ በኃላ የማቋቋም ስራ እደሚሰራ ተናግረዋል።
መሳይ ተክሉ
እሸቴ በቀለ