1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሶማሊያና ፀረ-ሽብር ዘመቻ

ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 27 2002

«---ለጊዜዉ መገመት የምችለዉ ግን የሽግግር መንግሥቱን ይበልጥ ማጠናከር ይፈልጉ ይሆናል።ከዚሕ በተጨማሪም ባለፉት አመታት እንዳየነዉ ቢያንስ ዩናይትድ ስቴትስ የሽግግር መንግሥቱን ማስታጠቅና በቀጥታ የአየር ድብደባ መፈፀም ሊሆንም ይችላል።»

https://p.dw.com/p/LLU3
የአሸባብ ታጣቂዎች-መቃዲሾምስል AP

05 01 10

ዩናይትድ ስቴትስና ብሪታንያ የፀረ-ሽብር ዘመቻቸዉን ሶማሊያ ዉስጥም ለማጠናከር በቅርቡ አስታዉቀዋል።ይሁንና ሥለዘመቻዉ አፈፃፀም ሁለቱ ሐገሮች በግልፅ ያስታወቁት ነገር የለም።ሶማሊያ ርዕሠ-ከተማ መቃዲሾ የሠፈረዉ የአፍሪቃ ሕብረት ሠላም አስከባሪ ሠራዊት (አሚሶም) ቃል አቀባይ እንደሚሉት ደግሞ ሶማሊያ ዉስጥ ምንም አዲስ ነገር የለም።የጀርመኑ የፖለቲካና የሳይንስ ጥናት ተቋም ባልደረባ አኔተ ቬበር በበኩላቸዉ ለሶማሊያ ከፀረ-ሽብር ዘመቻዉ ይልቅ ፖለቲካዊ መፍትሔ መፈለጉ ይመረጣል ባይ ናቸዉ።ነጋሽ መሐመድ ቤቨርን አነጋግሯቸዉ የሚከተለዉ ዘገባ አጠናቅሯል።

የዩናይትድ ስቴትስና የብሪታንያ ባለሥልጣናት ሰሞኑን በተደጋጋሚ እንዳስታወቁት የፀረ-ሽብር ዘመቻቸዉን ከየመን አልፎ እስከ ሶማሊያ ለማስፋፋት ወስነዋል።ሁለቱ ሐገሮች በተለይ ለሶማሊያዉ ዘመቻ የቀየሱት ሥልትና ገቢራዊነቱ ግን፥ የጀርመኑ የፖለቲካና የሳይንስ ጥናት ተቋም የምሥራቅ አፍሪቃ ጉዳይ የበላይ ወይዘሮ አኔተ ቬበር እንደሚሉት ግልፅ አይደለም።
«ጥሩ ጥያቄ ነዉ።(ዘመቻዉን) እንዴት በተግባር እንደሚፈፅሙት ዩናይትድ ስቴትስና ብሪታንያ እስካሁን በግልፅ ያስታወቁት ነገር የለም።ለጊዜዉ መገመት የምችለዉ ግን የሽግግር መንግሥቱን ይበልጥ ማጠናከር ይፈልጉ ይሆናል።ከዚሕ በተጨማሪም ባለፉት አመታት እንዳየነዉ ቢያንስ ዩናይትድ ስቴትስ የሽግግር መንግሥቱን ማስታጠቅና በቀጥታ የአየር ድብደባ መፈፀም ሊሆንም ይችላል።

ሁለቱ ሐገሮች የፀረ-ሽብር ዘመቻዉን በሶማሊያ እናጠናክራለን ያሉት አንዳድ የሶማሊያ ታጣቂ ሐይላት በተለይም አል-ሸባብ የአለም አቀፉ አሸባሪ ድርጅት የአል-ቃኢዳ ተባባሪ ነዉ።አል-ቃኢዳ ራሱም ሶማሊያ ዉስጥ መሸሸጊያ ያገኛል በሚል ምክንያት ነዉ።ወይዘሮ ቬበር እንደሚሉት ለሶማሊያ ችግር ፀረ-ሽብር ይሁን ሌላ ወታደራዊ ዘመቻ ዘላቂ መፍትሔ አይሆንም።
«የኔ ግምት የሶማሊያን ችግር በፀረ-ሽብር ዘመቻ መፈታት አይቻልም የሚል ነዉ።ምክንያቱም ከዚሕ ይልቅ እንዲያዉ ባጠቃላይ ለሕዝቡ መረጋጋትን ለማስፈን መጣሩ ነዉ ጠቃሚዉ።ባሁኑ ወቅት እርስ በራሳቸዉ የሚዋጉ የተለያዩ ወገኖች አሉ።እነኚሕ ማለት አለም አቀፍ አሸባሪነትን ኢላማ ያደረጉ አይመስሉም።ከዚሕ ጋር በተየያያዘ አሁን በሶማሊያ ያለዉን የፀጥታ ሁኔታ ሥመለከት አል-ሸባብን ብንወስድ፣-አል-ሸባብ ከሒዝቡል ኢስላም፥ ከሽግግር መንግሥቱ እና ከአፍሪቃ ሕብረት ጦር ጋር ነዉ የሚዋጋዉ።»

መቃዲሾ የሠፈረዉ የአፍሪቃ ሕብረት ሠላም አስከባሪ ሠራዊት (AMISOM- በእንግሊዝኛ ምሕፃረ-ቃሉ) ቃል አቀባይ ባርያጌ ባሁኩ በበኩላቸዉ ሶማሊያ በተለይም ርዕሠ-ከተማዋ ዉስጥ ከቃላት ጦርነት በስተቀር ብዙም የተለወጠ ነገር የለም-ባይ ናቸዉ።

«የጠመንጃዎችና የቃላት-ሁለት አይነት ዉጊያዎች አሉ።እዚሕ ከሚከናወነዉ ከሰባ እስከ ሰማንያ ከመቶ የሚሆነዉን የሚወስደዉ የቃላቱ ዉጊያ ነዉ።ከዚሕ በተቃራኒዉ ድልን በተመለከተ እርስ በርስ ከሚዋጉት ታጣቂዎች መካካል ምንም አይነት ለዉጥ ያየሁ አይመስለኝም።አሚሶም ከሰወስት አመት በፊት እዚሕ ከሠፈረበት ጊዜ ጀምሮ የታየ ተጨባጭ ለዉጥ የለም።»

18.07:2008 DW-TV Quadriga Annette Weber
አኔተ ቬበር «ዘላቂዉ ፖለቲካዊ መፍትሔ ነዉ»

ይሁንና በሶማሊያ ሠላም ለማስፈን የአፍሪቃ ሐገራት ተጨማሪ ወታደሮች እንዲያዘምቱ ራሱ የአፍሪቃ ሕብረት፥ የተለያዩ ድርጅቶችና ሐገራት እየጠየቁ ነዉ።እስካሁን ጦር ለማስዝመት ቃል ከገቡት ሐገራት እንኳን አብዛኞቹ ቃላቸዉን አላከበሩም።ምክንያት «ፀጥታ» ይላሉ ቬበር።

«የመቃዲሾን ሁኔታን ለሚያስተዉል ሰዉ-ስምንት ሺሕ ወታደሮች ለማዝመት ላቀደዉ ለአሚሶም (በርግጥ እስካሁን ወደ ስድስት ሺሕ አዝምቷል ይሕ ትልቅ ነዉ) የፀጥታዉ ሁኔታ በጣም አደገኛ ነዉ።ወታደሮቹ እንደ ሠላም አስከባሪ ሳይሆን የሚታዩት እንደጠላት ነዉ-የሚቆጠሩት፤ የሚጠቁትም።»

ወጣም ወረደ ሶማሊያን ሠላማዊት ሐገር ለማድረግ ትክክለኛዉ መፍትሔ «ፖለቲካዊ» ነዉ ይላሉ-ጀርመናዊቱ የአፍሪቃ ቀንድ ባለሙያ።ለሠላማዊ መፍትሔዉ ገቢራዊነት ጥያቄ «ያለዉ መልስ ግን» አሉ ቬበር «በጣም ትንሽ ነዉ»።ምክንያቱም ጉዳዩ ከሶማሊያ ተፋላሚ ሐይላት ዉጪ ኢትዮጵያ፥ ኤርትራን ጨምሮ የአካባቢዉን አለም አቀፍ ሐይላትንም የሚያጣቅስ ነዉና።
Interview mit Weber
Negash Mohammed
Shewaye Legesse