ስልጣን ያካፈለው የቡርኪና ፋሶ ጦር
ማክሰኞ፣ ኅዳር 16 2007የቀድሞው የቡርኪና ፋሶ ፕሬዚዳንት ኮምፖኦሬ ከስልጣን ከወረዱ ከአንድ ቀን በኋላ ቦታቸውን የተቆጣጠሩት ኢሳክ ዚዳ በዓለም አቀፍ ጫና ሲቪል ማህበረሰቡን ያካተተ የሽግግር መንግሥት ለመመስረት ተገደዋል።አዲሱ የቡርኪና ፋሶ ጠቅላይ ሚኒስትር ያኩባ ኢሳክ ዚዳ የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ብቻ ሳይሆኑ የመከላከያ ሚኒስትርም ናቸው። በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ቁልፍ የስልጣን ቦታ ከተቆናጠጡት ባለስልጣናት ውስጥ ምንም እንኳን አሁን የወታደራዊ የደንብ ልብሳቸውን ቢያወልቁም የጦር አዛዥ የነበሩት ኢሳክ ዚዳን በቅርብ ያገለግሉ እና ይታዘዙ የነበሩ እንደሆነ ይነገራል። ስለሆነም የዋጋዱጉ አመራር አሁንም በጦር ኃይል እጅ ይሆን? አይ ይላሉ በሀንቡርግ «ጊጋ » በተሰኘዉ የአፍሪቃ ጥናት ተቋም ባልደረባ የሆኑት አሌክሳንደር ስትሮህ ።«ከ20 በላይ ከሆኑት ከፍተኛ የሳይንስ እና የሲቪሉን ማህበረሰብ ከወከሉት መሐል ወታደሮቹ አራቱ ብቻ ናቸው ። »
የቡርኪና ፋሶ የሲቪሉ ማህበረሰብ ነው ከአንድ ወር በፊት አደባባይ ወቶ የቀድሞውን የሀገሪቱን ፕሬዚዳንት ብሌስ ካምፖዎሬን ከስልጣን ያስወረደው። ካምፖዎሬ ተጨማሪ ዘመን መግዛት እንዲችሉ የሐገሪቱ ሕገ-መንግሥት እንዲቀየር እና ለአምስተኛ የስልጣን ዘመን እንዲቀርቡ ለምክር ቤት ረቂቅ አቅርበው ነበር። ይህም ከ 27 ዓመታት የስልጣን ዘመን በኋላ መሆኑ ነው። ካምፖዎሬን ያልፈለገው የሀገሪቱ ህዝብ አደባባይ ወጥቶ ድምፁን በቁጣ በማሰማቱንም ፤ ካምፖዎሬ ከስልጣን ወርደው ወደ ኮት ዲቯር የሸሹት። ያኔም ዋና የጦር አዛዥ ኢሳክ ዚዳ ስልጣኑን ተቆጣጠሩ።
አሁን ዚዳ ከተቃዋሚዎች እና ሲቪል ማህበረሰቡ ጋር በአንድነት አዲስ ምርጫ ማካሄድ ይጠበቅባቸዋል።እድሉ ጠባብ አይደለም ይላሉ የአፍሪቃው ጥናት ተቋም ባልደረባ አሌክሳንደር ስትሮህ ፤« የሲቪሉ ማህበረሰብ እና የፖለቲካ ተቃዋሚዎቹ እስካሁን ገንቢ ሚና ነው የተጫወቱት። ከመጀመሪያው አንስቶ ከጦሩ ጋር መልካም ንግግር ነበራቸው። በዚህ መሰረት ሰው በቂ ዝግጅት የተደረገበት ምርጫ እንደሚካሄድ በተስፋ ወደፊት ሊመለከት ይችላል። ለማጣጣል አሁን ጊዜው አይደለም። ቢያንስ በአሁኑ ሰዓት ሲቪሎች ዋና ሚና ኖሯቸው እንደሚቆዩ መገመት ይቻላል።»
ቀድሞ አምባሳደር የነበሩት የአሁኑ የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ሚሼል ካፋንዶ በአዲሱ ካቢኔ ከፕሬዚዳንነት ስልጣን በተጨማሪ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትርነቱንም ቦታ ደርበው ይዘዋል። የምዕራብ አፍሪቃዊቷን ሀገር በሽግግሩ መንግሥት የአንድ አመት ዘመን ወደፊት አራምደው አዲስ ምርጫ ለማካሄድ ነው አላማቸው። ጊዜያዊው የሽግግር ምክር ቤት ደግሞ መንግሥትን መቆጣጠር አለበት ይላሉ ቤኔቬንዴ ሳታኒስላስ ሳንካራ፤ የተቃዋሚው ፓርቲ ሊቀመንበር። የተቃዋሚ ፓርቲዎቹ ግን መግባባት አልፈጠሩም። ኮምፓዎሬን ከስልጣን ያባረሩት በርካታ የህዝብ ንቅናቄ አራማጆች ወክለው ለምክር ቤቱ ስለሚልኩት ሰው እንኳን ሊስማሙ አልቻሉም። « በርካታ ድርጅቶች አሉ ሚና መጫወት የሚፈልጉ። ህግ ማውጫው ጋር ስንደርስ በመካከላችን ያለውን አለመስማማት ይዘን መቀጠል የለብንም።»ይላሉ ሳንካራ፤ « መልሶ መንቃት» የተባለው የተቃዋሚው ፓርቲ ሊቀመንበር።
አርድ ሪክማን/ ልደት አበበ
ነጋሽ መሀመድ