ማሊ፣ የለጋሽ ሀገራት ጉባዔ በአዲስ አበባ
ረቡዕ፣ ጥር 22 2005የማሊ ቀዉስ ላለፉት ሁለት ቀናት እዚያዉ አዲስ አበባ ተሰይሞ የነበረዉ የአፍሪቃ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ዋና ትኩረትም ነበር።ጉባኤዉ ትናንት ማምሻ ተጠናቅቃል።
ጌታቸዉ ተድላ ሐይለ ጊዮርጊስ ዝር ዝር ዘገባ አለዉ።
------
የሚከተለው ዘገባ የማሊን ውጊያ እና ወታደራዊ ጣልቃ ገብነትን ይቃኛል።
ከ1962 ጀምሮ ፈረንሳይ የጋቦን፥ የቻድ፥ የካሜሩን፥ የቡርኪና ፋሶ፥ የዛኢር፥ የኒዠር፥ የቱኒዚያ፥ የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ፥ የሩዋንዳ፥ የጅቡቲ እና የሌሎችም የቀድሞ ቅኝ ተገዢዎቿን አምባገነኖች ወይም አማፂዎችን በመደገፍ አፍሪቃ ዉስጥ ከሐምሳ ጊዜ በላይ ተዋግታለች።
ሠሜን ማሊ የሸመቁ ሙስሊም አማፂያንን የሚወጋዉ የፈረንሳይ ጦር፥ ድል፣ በድል እየተረማመደ ቅዳሜ፥ የግዛቲቱን ትልቅ ከተማ ጋዮ ተቆጣጠሮ ታሪካዊቷን ቱንቢክቱን ለመያዝ ከደጃፏ ደርሷል። በአዉሮጳ እና በአሜሪካ ሐያላን የፖለቲካ፣ የፕሮፓጋ፣ የሥንቅ-ትጥቅ ድጋፍ የተጠናከረዉ፣ በአፍሪቃዉን ወታደሮች የሚታገዘዉ የፈረንሳይ ጦር የበረሐማ-ግን ሥልታዊ፣ የደሐ ግን የማዕድን ሐብታሚቱን ሐገር ሙሉ ግዛት ከፓሪሶች እቅፍ የሚዶልበት ጊዜ ሩቅ አይደለም።ከዚያስ?-እንጂ ጥያቄዉ።ጥያቄዉ የወታደራዊ ጣልቃ ገብነትን ዓላማ፣ ሒደት ዉጤትን፣ የሚያጣቅስ-ሌላ ጥያቄ ማስከተሉ-እንጂ አነጋጋሪዉ።ላፍታ እንጠይቅ-እንነጋገር።
ለፈረንሳዊዉ የአፍሪቃ የፖለቲካ ጉዳይ አጥኚ ለፕሮፌሰር ሮናልድ ማርሻል ያቺን ጥያቄ-የወረወርኩት የዛሬ አሥራ-አምስት ቀን በዚሁ ዝግጅት ያልኩትን ለማስረገጥ ነበር።ለፕሬዝዳንት ኒኮላይ ሳርኮዝ ሊቢያ ከሌሎች የሚጋሯት አይቮሪኮስት ወይም ኮትዲቯር ግን በሌሎች፣ ፍቃድና ይሁንታ የብቻቸዉ ያደረጓት ነበረች።ፕሬዝዳንት ፍሯንሷ ኦሎንድ ደግሞ ከሌሎች የሚጋርዋት ሶሪያ ትሆን-ይሆናል።ማሊ ግን በሌሎች ድጋፍ፣ ፍቃድና ይሁንታ በርግጥ የብቻቸዉ ሆነች።
«ሙሉ በሙሉ እንደዚያ አይደለም።» መለሱ ፈረንሳዊዉ የፖለቲካ ሊቅ---ምክንያቱም እያሉ ቀጠሉም
«ምክንያቱም አይቪሪኮስትን የጀመሩት ሺራክ ናቸዉ።---ሳርኮዚ ጨረሱት---በማሊ ግን ልክ ነዉ ኦላንድ ሰም እያገኙ ነዉ።»
እነሱ-ይቀያየራሉ።የወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ዓላማ-መርሕን ግን ይወራረሳሉ፥ አንዱ የጀመረዉን ሌላዉ ካለበት ዘመን-ወግ ፈሊጥ ጋር እያጣጠመ ስም-እየሰጠ-ስም አግኝቶ ይቀጥላል-ወይም ይፈፅመዋል።
በሺሕ-ሥልሳ ስድስት (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ፈረንሳይና ብሪታንያ ሐስቲንግስ ላይ የገጠሙት ጦርነት በፈረንሳዮች ድል አድራጊነት መጠናቀቁ ለአሸናፊዎቹ ታላቅ ኩራት ማጎናፀፉ፣ ተሸናፊዎቹን ከፍተኛ ሐፍረት ማከናነቡ አላጠያየቅም።
የኩራት ሐፍረቱ ተቃርኖ ድል አድራጊዎች አዉሮጳን ከዚያም አልፈዉ ድፍን ዓለምን መግዛት አለብን ከሚል እብሪት፣ ድል-ተደራጊዎችን እንዴት እንሸነፋለን ከሚል-የበቀል ቁጭት ዶሎ ለሌላ ጦርነት ከመዘጋጀት ባለፍ ለአዉሮጳም-አዉሮጳ ለመራችዉ ዓለምም ሠላም የተከረዉ የለም።
እብሪት ብቀላዉ ሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት እስከተፈፀመበት ጊዜ ድረስ አዉሮጳን ካንዱ ጦርነት ሳታገግም ከሌላ ጦርነት እየማገደ፣ ሌላዉ ዓለምን እያነደደ ዘመናት አስቆጥሯል። ወደ ዘጠኝ መቶ ዓመት ባስቆጠረዉ ዘመን የብሪታንያዉ ማሰራጫ ጣቢያ ቢቢሲ እንደዘገበዉ አዉሮጳ ሐምሳ-ሰወስት ትላልቅ ጦርነቶችን አስተናግዳለች።
ከሐምሳ ሰወስቱ፥ በአርባ-ዘጠኙ ትላልቅ ጦርነት፣ ወይም አንድ መቶ ሰማንያ አምስት ሥፍራ በተደረጉ ዉጊያዎች ፈረንሳይ በቀጥታ ተካፍላለች።ከአንድ መቶ ሰማንያ-አምስቱ ዉጊያ አንድ-መቶ ሰላሳ ሁለቱን የፈረንሳይ ጦር አሸንፏል።አርባ-ሰወስት ጊዜ ተሸንፏል።በተቀሩት አስሩ-በኳስ ግጥሚያ ቋንቋ-«አቻ ወጥቷል።»
ፈረንሳይና ጀርመን ባለፈዉ ሳምንት ለሐምሳኛ ዓመት ያከበሩት የወዳጅነት ስምምነት፣(በቀድሞዋ ይጎዝላቪያዉ አንዴ ከተከሰተዉ በስተቀር) አዉሮጳና አዉሮጳዉያን የመሠረቱት ሰሜን አሜሪካ-ጦርነትንና ከጦርነት የሚዶሉ እብሪት፣ብቀላዎችን እርግፍ አድርገዉ የመተዋችዉ፣ አለመግባባቶችን በዉይይት እየፈቱ ትብራቸዉን የማጠናከራቸዉ የቅርብ ጉሉሕ ምስክር ነዉ።
የጦርነት መጥፎ ዉጤት ለማወቅ በጦርነት መሐል ማለፍ አያስፈልግም።የጀርመኗ መራሒተ-መንግሥት የሰብአዊ መብት ጉዳይ አማካሪ ጉተር ኑከ እንደሚሉት ደግሞ ለፍጡራን ሕልዉና የሚጨነቅ ከጦርነት ጨርሶ አይገባም።
«ሁለንተናዊ የሠብአዊ መብት ፅንሰ ሐሰብን ከልቡ የተቀበለ ምንጊዜም ጦርነት አያደርግም። ምክንያቱም ጦርነት በተደረገ ቁጥር ሕይወት ሥለሚጠፋ፥ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት ሥለሚፈፀም።ያም ሆኖ ፖሊስ ያስፈልጋል። አንዳዴ የሐይል እርምጃ ይወሰዳል።»
ፕሬዝዳንት ሻርልስ ዶጎልና መራሔ መንግሥት ኮንራድ አደናወር ዛሬ ለአዉሮጳ ሠላም፥ አድነት፥ የጋራ ብልፅግና መሠረት የጣለዉን ሥምምነት በ1963 መፈራረማቸዉ ከአስከፊዉ ጦርነት የመማራቸዉ፥ ኑከ እንዳሉት የሰብአዊ መብትን ሁለንተናዊ ፅንሠ-ሐሳብ ገቢር ለማድረግ የመወሰናቸዉ አብነት ነበር።
ይሁንና ስምምነቱ ከመፈረሙ በፊትና በሚፈረምበትም መሐል ፥ከኮሪያ እስከ ቬትናም ከአልጄሪያ እስከ ጋቦን፥ ከኩባ እስከ ምሥራቅ ጀርመን የነበረዉ ጦርነት፥ ግጭትና ፍጥጫ የሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ተዋጊዎች ለራሳቸዉ ሠላም፥ ሰብአዊነት፥ ትብብር፥ ብልፅግናን ለማስረፅ ከመወሰን መጣራቸዉ እኩል እንደገና ኑከ እንዳሉት ሌላዉን ዓለም እንደ ፖሊስ ለመቆጣጠር መፈለግ-ማቀዳቸዉን-ጠቋሚ፥ በጦርነት የኖረዉ ዓለምም በጦርነት የመቀጠሉ ምልክት ነበር።
የፈረንሳይና የጀርመን የወዳጅነት ስምምነት የብር ኢዮቢሊዮ በዓል ሲከበር የፈረንሳይ ጦር ሰሜናዊ ማሊን ከሚያተራምሰዉ ጦርነት መግባቱ ደግሞ ከአሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ማግሥት አዉሮጳና ሰሜን አሜሪካን ላይ ሠላም ሲሰርፅ ሌላዉ ጋ የቀጠለዉ ጦርነት ዛሬም ያለማባራቱ አብነት አይሆንም ማለት አይቻልም።
የፈረንሳይ ጦር ማሊ ላይ የሚወጋቸዉ አማፂያን አሸባሪዎች አለያም ጂሐዲስት መሆናቸዉን ያልመሰከረ-የለም።ካለም የሚሰማዉ የለም።አሸባሪዎች ደግሞ መጥፋት አለባቸዉ።እና ፕሬፌሰር ማርሻል እንደሚሉት የፈረንሳይ ጦር ዘመቻ ተገቢ ነዉ።
«ሁኔታዉ ምንድ ነዉ ጂሐዲስቶች ራሳቸዉ ሲቫሬ፥ ኮና እና ምብቲ ላይ ጥቃት ከፍተዋል።ይሕ አፀፋ ያስፈልገዋል።የማሊም ሆነ የኢኮዋስ ጦር ለጥቃቱ አፀፋ ለመስጠት አልቻሉም።ሥለዚሕ የፈረንሳዮች አርፈዉ ቢቀመጡ ኖሩ ምን-ይሆን ነበር።»
ጥያቄዉን ዛሬ መመለስ በርግጥ ይከብዳል።እንዲያዉ ለግምቱ ያሕል፥- ምናልባት እንደ ፈረንሳዮች ኮት-ከራቫት የሚያጠልቁት የባማኮ ገዢዎች እንደ ቱአሬጎች ወይም እንደ አረቦች ጀላቢያ ባጠለቁ፥ በጠመጠሙ፥ ጢማም ገዢዎች ይቀየሩ ነበር።ምናልባት የባማኮ ገዢዎችና የቱአሬግ አማፂያን ይታረቁ ይሆናል።ምናልባት ማሊ ኢራቅን፥ አፍቃኒስታንን ሊቢያን ትቀላቀል-ይሆናል።ምናልባት---ሌም ሰበብ መስጠት ይቻላል።
እርግጡ ግን-የፈረንሳይ ጦር ማሊ-ለመዝመት፥ መዋጋቱ የተሰጠዉ ምክንያት የጂሐዲስቶችን አደጋ ማስወገድ የሚል መሆኑ ነዉ።የፈረንሳይ ቅኝ ገዢ ጦር በ1954 ዲየን ቢየን ፉ ላይ እስከተሸነፈበት ጊዜ ድረስ እንዲሕ እንዳሁኑ በአሜሪካና በምዕራብ አዉሮጶች ርዳታ ቬትናሞቹን ለመዉጋቱ የተሰጠዉ ሰበብ ምክንያት «ኮሚንስቶችን ማስወገድ» የሚል ነበር።
ዩናይትድ ስቴትስ እዚያዉ ቬትናም፥ ከቬትናም በፊት ደግሞ የኢትዮጵያን ጨምሮ የገሚስ ዓለምን ጦር አስከትላ ኮሪያ ለመዝመት-መዋጋትዋ የተሰጠዉ ምክንያትም «የኮሚንስቶችን ሥጋት ማስወገድ» የሚል ነበር።እንደ እዉነቱ ከሆነ ኮሚንስቶች ይወገዱ የነበረዉ የፈረንሳይ ጦር በ1962 ተሸንፎ እስከ ወጣበት አልጄሪያዎችን ሲወጋ፥ ሰሜን አፍሪቃዊቱን አረባዊት ሐገር በማጥፋቱ፥ ወይም የሕዝብ ነፃነትን በመደፍለቁ ከመከሰስ-መወቀሱ ይልቅ «ሸፍቶችን ለማጥፋት» በመፋለሙ ሲደነቅ-ሲወደስ ነበር።
ከ1962 ጀምሮ ፈረንሳይ የጋቦን፥ የቻድ፥ የካሜሩን፥ የቡርኪና ፋሶ፥ የዛኢር፥ የኒዠር፥ የቱኒዚያ፥ የማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ፥ የሩዋንዳ፥ የጅቡቲ እና የሌሎችም የቀድሞ ቅኝ ተገዢዎቿን አምባገነኖች ወይም አማፂዎችን በመደገፍ አፍሪቃ ዉስጥ ከሐምሳ ጊዜ በላይ ተዋግታለች።ለየጣልቃ ገብ ዘመቻ-ዉጊያዋ ከየዘመኑ ወግ ጋር የሚጣጠም ሰበብ ምክንያት ሰጥታለች።በወዳጆችዋ ተደግፋለች።
ሺራክ ጀምረዉት ሳርኮዚ ለጨረሱት ለኮትዲቯሩ ዘመቻ የተሰጠዉ ሰበብ ምክንያት አምባገነን መሪን አስወግዶ በሕዝብ የተመረጡትን ሥልጣን ማስያዝ ነበር።ለሊቢያዉ ድብደባ አማላይ ሰበብ ምክንያት ተበጅቶለታል።ለማሊዉ ዉጊያም «አሸባሪዎችን ማጥፋት» የሚል ቀልብ-ጆሮን ሳቢ ምክንያት መስጠቱ አልገደደም።ጥያቄዉ አምና እና ሐቻምና ማሊ ላይ የማይታወቁት አሸባሪዎች በመንፈቅ እድሜ ከየት መጡ ነዉ።
የሩሲያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ ከሊቢያ የሚል አጭር መልስ አላቸዉ።ላቫሮቭ ባለፈዉ ሳምንት እንዳሉት አልጄሪያ ዉስጥ በርካታ ሰዎችን አግተዉ የነበሩት አሸባሪዎች በሊቢያዉ ጦርነት ምዕራባዉያን ሐገራት ከጎናቸዉ አሰለፋዋቸዉ የነበሩት ሐይላት ናቸዉ።ሰሜን ማሊ የሸመቁት ደግሞ የቃዛፊ ጦር ባልደረቦች።
ፕሮፌሰር ማርሻልም ተቀራራቢ መልስ አላቸዉ።
«በርካታ ቱአሬጎች፥ ቱአሬጎች ብቻ ሳይሆኑ ሌሎችም፥ ግን ያዉ ባብዛኛዉ ቱአሬጎች ከሊቢያ ከባድ ዘመናይ ጦር መሳሪያና ጥይት ታጥቀዉ ማሊ ገብተዋል።ብዙዎቹ የማሊ ጦርን መቀላቀል ፈልገዉ ነበር።ጦሩ ግን ቀድሞ ፈረሰ።እነሱም አልተደራጁም ነበር።በዚሕ መልኩ ሲታይ የሊቢያዉ ቀዉስ አሁን ሠሜን ማሊለ ለምናያቸዉ አማፂያን እግረኛ ጦር አበርክቷል።»
የሊቢያዉ ጦርነት የረጅም ጊዜ፥ አካባቢያዊ መዘዝ ባለመጤኑ ዛሬ ማሊ በጦርነት ትነዳለች።ሕዝቧ ያልቃል፥ ይሰደዳል፥ ይፈናቀላልም።ከማሊዉ ዉጊያ ቀጥሎ የሚሆነዉን የሚያዉቅ የለም።የፈረንሳይ ጦር የሚወጓቸዉ አማፂያን ግን ባብዛኛዉ ወደ ሊቢያ እየተመለሱ ነዉ።
ከሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ማግሥት ጀምሮ የዋሽግተን፥ የሞስኮ፥ የፓሪስ፥ የለንደን ሐያላን በየፊናቸዉ በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ በሚመሩት ወታደራዊ ፖለቲካዊ ጣልቃ-ገብነት በየዘመኑ የነበረ ጥቅማቸዉን ማስከበር ችለዋል።
ኮኮሪያ እስከ ቬትናም፥ ከመካከለኛዉ ምሥራቅ እስከ አፍሪቃ፥ ከኩባ እስከ አፍቃኒስታን፥ ከሶማሊያ እስከ ኮትዲቯር፥ ከኢራቅ እስከ ሊቢያ ጣልቃ በተገባ ቁጥር ጊዚያዊ ጥቅምን ከማስከበር ባለፍ ጣልቃ-የሚገባበትን ትክክለኛ ምክንያት፥ የዉጊያዉን ዉጤት፥ የረጅም ጊዜ ተፅዕኖዉን ለማጤን አለመፈለጋቸዉ ግን ዓለምን በተለይ አፍሪቃና እስያን ከጦርነት አዉድ ሆነዉ እንዲቀሩ አስገድዷቸዋል።
ከቀዝቃዛዉ ጦርነት ፍፃሜ በተለይም ከአሜሪካ መራሹ የአፍቃኒስታን ዘመቻ ማግሥት እንዳዲስ በተያዘዉ ሥልት መሠረት ከዳርፉር እስከ ሶማሊያ፥ ከኢትዮጵያ እስከ ኤርትራ፥ ከኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ እስከ ላይቤሪያ፥ አሁን ደግሞ እስከ ማሊ በተለጠጠዉ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት የአፍሪቃ ሐገራት ተሳትፎ ጨምሯል።የአፍሪቃ መሪዎች ለአፍሪቃዉያን ችግር አፍሪቃዊ መፍትሔ ማለታቸዉ አልቀረም።
የአፍሪቃ መሪዎች የየራሳቸዉን ሕዝብ በብረት ጡጫ-እየቀጠቀጡ የሌዉ አፍሪቃዊ ችግር ያስጨንቀናል ማለታቸዉ ከማሳዘን፥ ማስተዛዘቡ አልፎ-ብዙዎችን ያስፈግጋል።
እንዲያም ሆኖ አፍሪቃዉያን በራሳቸዉ የጋራ ስምምነት፥ ለሕዝባቸዉ ሠላምና ደሕንነት ጦር ያዘመቱ፥ ያዋጉ፥ ሠላም ያስከበሩበት ጊዜ የለም። ካለም ከቁጥር የሚገባ አይደለም።የማሊዉ ዘመቻ ሲነገር፥ ሲታቀድ፥ የምዕራብ አፍሪቃ የኢኮኖሚ ማሕበረሰብ (ኢኮዋስ) አባል ሐገራት ጦር የሚያዘምቱት የድርድሩ አማራጭ ካልተሳካ ብቻ ነዉ ተብሎ ነበር።ድርድሩ በቀጠሮ እንደተንጠለጠለ ፈረንሳዮች አፍሪቃዉያኑን ቀድሞ ከአፍሪቃዊቱ ማሊ ገቡ።
ሮናልድ ማርሻል ፈረሳዮች ምክንያት-ያሉትን ምክንያት ይናገራሉ።
«ባለፉት ወራት የሆነዉ ችግሩን በድርድር ለመፍታት አልጀሪያ የተለያዩ ሙከራዎችን አድርጋለች።ብዙ ጊዜ ግን ለድርድር አልጀሪያ የሚሔዱት የአማፂያኑ መልዕክተኞች ከንቅናቄያቸዉ ተጨባጭ አቋም ይልቅ የአልጀሪያን ፍላጎት ማንፀባረቁን ነዉ-የወደዱት።ይሕ አንዱ ነዉ።ሁለተኛዉ ለመደራደር ከፈለጉ የመፍቲ ከተማን ለምን አጠቁ።ይሕ ጥቃት አልጄሪያዎች የፈረንሳይ የጦር አዉሮፕላኖች በአየር ክልላቸዉ እንዲበር በመፍቀድ የፈረንሳይን ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ደግፈዋል።»
የአፍሪቃ ሕብረትና ኢኮዋስን የወከሉት አደራዳሪ ግን አልጄሪያ ሳትሆን የኮትዲቯሩ ፕሬዝዳት ብሌስ ኮፓወሬ ነበሩ።ኮምፓወሬም ሆኑ ሌሎቹ የአፍሪቃ መሪዎች የድርድሩ ሒደት ባልተፈለገ አቅጣጫ መሔዱ፥ አስከፊዉ ጦርነት መጋሙ፥ በፈረንሳይ መቀደማቸዉ አላስጨነቃቸዉም።ፈረንሳይን ለማመስገን ግን እየተሸቀዳደሙ ነዉ።
እስከ ትናንት ድረስ የአፍሪቃ ሕብረትን የሊቀመንበርነት ሥልጣን ይዘዉ የነበሩት የቤኒኑ ፕሬዝዳት ቶማስ ያዬ ቦኒን በጣም ያሳሰባቸዉ ደግሞ የፈረንሳይ ጦርን የሚያግዘዉ የኢኮዋስ ጦር ፈጥኖ አለመዝመቱ ነዉ።ፈጠነም-ዘገየ የአፍሪቃ ሕብረት፥ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትም እንዲዘምት የወሰኑት የኢኮዋስ አባል ሐገራት ጦርን ነበር።ቀድሞ የዘመተዉ ግን የፈረንሳይ ጦር ነዉ።የፈረንሳይ ጦርን ቀድሞ የተከተለዉ ደግሞ የኢኮዋስ አባል ያልሆነችዉ ግን የቀድሞ የፈረንሳይ ቅኝ ተገዢ የቻድ ጦር ነዉ።
ለምስቅልቅሉ ጦርነት መስቅልቅል መፍትሔ።አሸባሪን የማጥፋት፥ ማሊን የማረጋጋቱ ዘመቻ-እንዲሕ ቀጥሏል።የአፍሪቃ ሠላም፥ የዓለም ፀጥታ፥ የሕዝብ ደሕንነት፥ መብት ነፃነትም-እንዲሁ።ከዚያስ? ትናንት ተጠይቆ-ነበር።ዛሬም ይጠየቃል።ነገም።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ለመድገም ያብቃን።
ነጋሽ መሐመድ
ሒሩት መለሰ