ማሊና የአንድነት መንግሥት ምሥረታ
ረቡዕ፣ ሐምሌ 25 2004
የብሔራዊ አንድነት መንግሥት እንዲመሠርት ኤኮዋስ አስቀምጦት የነበረው ጊዜ ገደብ ትናንት እአአ ማክሰኞ ሐምሌ 31፣ 2012 ዓም አልፎዋል። የዶቼ ቬለዉ አድሪያን ክሪሽ እንደዘገበው፡ የማሊ የሽግግር መንግሥት ፕሬዚደንት ዲዮንኩንዳ ትራውሬ የኤኮዋስን ጥያቄ ለማሟላት ከፍተኛ ጥረት ቢያደርጉም፡ የራሳቸውን ጥቅም ማስጠበቅ የሚፈልጉ ብዙ አንጃዎች በመኖራቸው፡ ጥረታቸው በዚሁ የጊዜ ገደብ ውስጥ መሳካቱ አጠራጣሪ ሆኖዋል።
ከመፈንቅለ መንግሥት አካሄጆች የጦር ኃይል አባላት ጥቃት ከተጣለባቸው በኋላ ያለፉትን ሁለት ወራት በፓሪስ ፈረንሳይ ሲታከሙ ቆይተው ባለፈው ዓርብ፡ ሐምሌ 27፣ 2012 ዓም ወደ ሀገራቸው የተመለሱት ከተመሰረተ 4 ወሩ የሆነው የማሊ የሽግግር መንግሥት ፕሬዝዳንት ዲዮንኩንዳ ትራዎሬ የብሔራዊ አንድነቱን መንግሥት ምሥረታ ኃላፊነት ራሳቸው እንደሚይዙ ባለፈው እሁድ በቴሌቪዝን ባደረጉት ንግግር አስታውቀዋል። የተለያዩትን ኃይላት የሚያጠቃልል የብሔራዊ አንድነት መንግሥት በማሊ በወቅቱ የሚታየውን የፖለቲካ ቀውስ በተሻለ መንገድ ሊያበቃ እንደሚችል ኤኮዋስ ይገምታል። ትራዎሬ የኤኮዋስን ጥያቄ ለማሟላት ሁለት አዳዲስ የሽግግሩ መንግሥት ምክትል ፕሬዚደንቶችን ሰይመዋል። ብዙ የመገናኛ ብዙኃን ይህንኑ የትራዎሬን ርምጃ ወቅታዊው የሀገሪቱን ጠቅላይ ሚንስትር ሼክ ሞዲቦ ዲያራን ሥልጣን አልባ ያደረገ ብለውታል። ትራውሬ በፈረንሣይ ሀገር በነበሩባቸው ሁለት ወራት ጠቅላይ ሚንስትሩ የሀገሪቱን ሁኔታ አላላሻሻሉም፤ በሰሜናዊ ማሊ የቀጠለውን ውዝግብም አላበቁም በሚል ዲያራ ሥልጣናቸውን እንዲለቁ በርካታ የማሊ ታዋቂ የፖለቲካ ፓርቲዎችና የሲቪል ማህበራት መጠየቃቸው ይታወሳል። ይሁንና፡ ዲያራ ለዶይቸ ቬለ በሰጡት ቃለ ምልልስ ፕሬዚደንት ትራዎሬ ባልነበሩበት ጊዜ ስለማሊ ሁኔታ ሙሉ መረጃ እንደነበራቸው ነው የገለጹት።
« አሁን እየቀረበ ያለውን መላ ምት ልረዳው አልቻልኩም። ከሥልጣን ተባርሬ ቢሆን ኖሮ፡ ፕሬዚደንቱ በግልጽ ይነግሩኝ ነበር። በአሁኑ ጊዜ መፍትሔ ልናገኝላቸው የሚገቡ ሌሎች አሳሳቢ ችግሮች አሉ። እነዚህ ችግሮች መፍትሔ ካገኙ በኋላ፡ ጠቅላይ ሚንስትሩ ከሥልጣን መባረር አለመባረሩን ለማየት እንችላለን። »
የሽግግሩ መንግሥት ፕሬዚደንት ትራውሬ በማሊ በቅርቡ የብሔራዊ አንድነት መንግሥት የማቋቋም ከባድ ኃላፊነት እንደሚጠብቃቸው ነው ዲያራ ያስረዱት። ይሁንና፡ የተለያየ ጥቅማቸውን ለማስከበር የሚጥሩትን የተለያዩ ቡድኖችን በአንድ ጠረጴዛ ዙርያ ማወያየቱ እጅግ አዳጋች እንደሆነ ይገኛል። ባንድ በኩል፡ የቀድሞውን ፕሬዚደንት አማዱ ቱማኒ ቱሬን በሰሜን ማሊ የሚንቀሳቀሱትን የቱዋሬግ ዓማፅያንን ትግል ማብቃት አልሆነላቸውም በሚል ባለፈው መጋቢት ሀያ ሁለት፣ 2012 ዓም የመፈንቅለ መንግሥት ያካሄደውና ያንዳንድ ፓርቲዎች ድጋፍ ያለው በሻምበል ሳኖጎ የሚመራው የጦር ኃይል ቡድን፡ በሌላ በኩል ደግሞ ተቃዋሚዎቹን ማቀራረብ አልተቻለም። በደቡብ አፍሪቃ የዓለም አቀፉ ፀጥታ ጥናት የፖለቲካ ተንታኝ ዴቪድ ዙማኑ እንዳስረዱት፡ የሳኖጎ ቡድን ሕገ መንግሥቱን በመፃረር ሥልጣኑን የሙጥኝ ብሎ ለመቆየት ይፈልጋል፤ ግን፡ የብዙዎቹ ሲቭል ማህበረሰቦች ድጋፍ ያለው የመፈንቅለ መንግሥቱ ተቃዋሚዎች ይህንን ዕቅዱን አልደገፉትም።
ሰሜን እና ደብብ ማሊ ወደፊትም በሀይማኖትን መሠረት ያላደረገ መንግሥት የሚኖራት ሀገር ሆና መቆየት አለባት በሚለው ሀሳብ ላይ ግን ተቀናቃኞቹ ወገኖች ይስማማሉ። ይሁንና፡ በሰሜናዊ ማሊ የሚንቀሳቀሱት የአዛዋድ ነፃነት ብሔራዊ ንቅናቄ፡ በምህፃሩ የኤም ኤን ኤል ኤ ተዋጊዎች በማሊ በሚቋቋም የብሔራዊ አንድነት መንግሥት ውስጥ እንደማይጠቃለሉና ነፃ መንግሥት የማቋቋም ዕቅድ እንዳላቸው ነው ደጋግመው ያስታወቁት። ግን፡ ኤምኤን ኤልኤ የማሊ ቱዋሬጎችን በጠቅላላ እንደማይወክል ያስታወቁት ዴቪድ ዙማኑ፡ የማሊን ውዝግብ ሊያበቃ የሚችለው የፖለቲካ መፍትሔ ብቻ መሆኑን አስረድተዋል።
«ምርጫ ብቻ ነው በማሊ የሚኖረውን ሕዝብ በጠቅላላ የሚወክል እና የሀገሪቱንም አንድነት የሚያስገኘው። በኔ አስተሳሰብ ይህ ነው ወደፊት የሚቋቋመው መንግሥት ዋነኛ ተግባር መሆን ያለበት።»
የሽግግሩ መንግሥት ፕሬዚደንት ትራውሬም ሆኑ ምክትሎቻቸው ወይንም ሚንስትሮቻቸው፡ አንዳቸውም በሀገሪቱ በሚደረገው ፕሬዚደንታዊ ምርጫ ላይ እንደማይሳተፉ አስታውቀዋል።
አድሪያን ኪርኽ/አርያም ተክሌ
ተክሌ የኋላ