ማሊና የሰላም ማፈላላጉ ጥረት
ቅዳሜ፣ ኅዳር 1 2005
ማሕበሩን ወክለዉ የማሊን ተፋላሚዎች የሚሸመግሉት የቡርኪና ፋሶዉ ፕሬዝዳት ብሌዝ ኮምፓዎሬ ሰሜናዊ ማሊን ከያዙት አክራሪ ሙሥሊም ሚሊሺያዎች መካከል አንዱ ከሆነው አንሳር ዲን ጋር ባለፈው ማክሰኞ ተወያይተው ነበር። ከዚሁ ውይይት በኋላ የአንሳር ዲን ቃል አቀባይ መሀመድ አህራቢ በቡርኪና ፋሶ መዲና ዋጋዱጉ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፡ ቡድናቸው የሚያካሂደውን ውጊያ እንደሚያቆም አስታውቀዋል።
« መተማመን ለሚፈጠርበትና የፀጥታው ሁኔታም አስተማማኝ ለማድረግ ሲል የአንሳር ዲን ተልዕኮ ውጊያውን ሙሉ ለሙሉ ለማቆም፡ ሰውና ዕቃ፡ የሰብዓዊ ርዳታ ጭምር በነፃ የሚዘዋወርበትንም ዋስትና ለመስጠት ዝግጁ ነው። ከዚህ በተጨማሪ፡ የአንሳር ዲን ቡድን ማንኛውንም ፅንፈኝነትና አሸባሪነት እርግፍ አድርጎ መተውን እና ድንበር ሳይገድበው የሚካሄድ የተደራጀውን ወንጀል እንደሚታገል ያስታውቃል። »
የአንሳር ዲን እና የሌላ የቱዋሬግ ዓማፅያን ቡድን ካለፈው ሚያዝያ ወዲህ ሰማናዊ ማሊን በመቆጣጠር በዚሁ በቆዳ ስፋቱ ፈረንሣይን በሚያህለው አካባቢ እሥላማዊውን የሸሪአ ሕግ በእነሱ አተረጓጎም በማስተዋወቅና የኃይል አገዛዝ በማስፋፋት፡ ያካባቢው ነዋሪዎች ሙዚቃ እንዳይሰሙ ከልክለዋል፤ በትዳራቸው ላይ የሚማግጡ በድንጋይ ይወገራሉ፤ የሱስ አስያዡ ዕፅ እና የጦር መሣሪያ ንግድንም ከልክለዋል።
እነዚሁ የአንሳር ዲን ሚሊሺያዎች አሁን ፅንፈኝነትን፡ ሽብርን እና ከድንበር ባሻገር የሚፈፀመውን ወንጀል ማውገዛቸው እና የተኩስ አቁም ለማድረግ መስማማታቸው ብዙ የፖለቲካ ታዛቢዎችን አስገርሞዋል። እንደ ማሊው ተወላጅና የፖለቲካ ተንታኝ ሴጋ ጉንዲያም አንሳር ዲን እና ሌሎቹ በሰማናዊ ማሊ የሚንቀሳቀሱት ፅንፈኛ ቡድኖች አቋማቸውን በየጊዜው የሚለውጡ በመሆናቸው አይታመኑም።
« አንሳር ዲን ባለፉት ዓመታት ከዕፀ ሱስ እና ከጦር መሣሪያው ሕገ ወጥ ንግድ እጅግ ብዙ ገንዘብ አግኝቶዋል። ይህንኑ ገቢያቸውን ከፍ ለማድረግ ቢችሉ ደስ ይላቸዋል። ካልቻሉ ግን ቢያንስ አሁን ደረስነው ባሉት የሰላም ውሳኔ ይህንኑ የሰበሰቡትን ገንዘብ ለማዳን ጥረት ጀምረዋል። በሰሜናዊ ማሊ የሚጀመር ጦርነት ይህን ያካበቱትን ሀብት ሁሉ ያሳጣቸዋልና። »
የአንሳር ዲን መሪ ኢያድ አግ ጋሊ ከማሊ ቀውስ ተጠቃሚ ሆኖዋል። ጋሊ የቱዋሬግን ዓማፅያን በሰሜናዊ ማሊ የራሳቸውን ነፃ መንግሥት እንዲያቋቁሙ ከብዙ አሠርተ ዓመታት ወዲህ ሲመራ ከቆየ በኋላ፡ ባካባቢው እየተጠናከሩ የመጡትን አክራሪ ቡድኖች ተቀላቅሎዋል። በዚሁ ርምጃው የተነሳም አንሳር ዲን ሰላም ለመፍጠር ያሳየው ዝግጁነትን ይጠራጠሩታል።
« አጋ ጋሊን በግል አውቃቸዋለሁ። በጣም ዘዴኛ ሰው ናቸው። እና አዲስ ያገኙትን ቁልፍ ሥልጣን በመጠቀም በወቅቱ ተፅዕኖዋቸውን ለማሳደግ እየሞከሩ ነው። ምክንያቱም አንሳር ዲን በሰሜናዊ ማሊ ከሚንቀሳቀሱት ሌሎቹ ሙሥሊም ቡድኖች፡ ለምሳሌ ከሙዣዎ ጋ ጥሩ ግንኙነት የለውም። ሙዣዎ አንሳር ዲን በሚቆጣጠረው አካባቢ በተደጋጋሚ ጥቃት ሰንዝሮዋል።»
የማሊ ጦር እነዚህን የተለያዩ ሙሥሊም ቡድኖችን፡ አንሳር ዲንና ሙዣዎን በኃይል ለማባረር ይፈልጋል። እና በሙውሊሞቹ የተያዘውን ሰሜናዊ የሀገሩን ከፊል ለማስለቀቅ የሚቻልበትን ዕቅድ ለማውጣት ከብዙ ሣምንታት ወዲህ ከምዕራብ አፍሪቃ መንግሥታት የኤኮኖሚ ማሕበረሰብ፡ ኤኮዋስ፡ ከተመድ፡ ከአፍሪቃ ህብረት እና ከአውሮጳ ህብረት ከፍተኛ የጦር ባለሥልጣናት ጋ በመዲናው ባማኮ መክረው አንድ ዕቅድ ማውጣታቸውን የአንሳር ዲን ተደራዳሪዎች ውጊያ እንደሚያቆሙ በዋጋዱጉ፡ ቡርኪና ፋሶ ካስታወቁ ከጥቂት ሰዓታት በኋላ በይፋ ገልጸዋል። ኤኮዋስ በዕቅዱ መሠረት፡ ወደ ሰሜናዊ ማሊ 4000 ወታደሮች ለመላክ ይፈልጋሉ። የተመድ ፀጥታ ጥበቃ ምክር ቤት ይህንኑ የጦር ተልዕኮ ዕቅድ በዚህ በያዝነው የህዳር ወር መጨረሻ ገደማ ማፅደቅ ይኖርበታል። ይህን ዓይነቱን ዕቅድ ሊደግፍ እንደሚችል የፀጥታው ምክር ቤት ዝግጁነቱን የገለጸው ባለፈው ወር አጋማሽ እንደነበር አይዘነጋም። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በዚሁ ውሳኔው የሰማናዊ ማሊ የሚታየው ቀውስ ማሊን ብቻ እንደማይመለከት መገንዘቡን አሳይቶዋል ያሉት የማሊ መከላከያ ሚንስቴር አማካሪ ኪስማ ጋጉ የአውሮጳ ህብረትም ተልዕኮውን እንደሚደግፍ ተስፋቸውን ገልጸዋል።
« የማሊ ጉዳይ ብቻ አይደለም። የአውሮጳ ፀጥታንም የሚመለከት ነው። »
ሰሜናዊ ማሊ የዓለም አቀፉ ሽብርተኝነት መናኸሪያ እንዳትሆን የሰጋው የአውሮጳ ህብረት ለተልዕኮው የትጥቅና ስንቅ፡ እንዲሁም፡ የገንዘብ ድጋፍ ለመስጠት፡ ከዚህ በተጨማሪም የማሊን ጦር ለማሠልጠን ቃል ገብቶዋል።
ይሁንና፡ ኤኮዋስ ባንድ በኩል የጦር ተልዕኮ ለመላክ እያቀደ፡ በሌላ ወገን ከሙሥሊሞቹ ጋ ድርድር ማካሄዱን ብዙዎች ቢያጠያይቁም፡ የፖለቲካ ተንታኙ ሴጉ ጉንዲያም የዚህኑ ሁለትዮሽ ሙከራ ምክንያት እንደሚከተለው ገምተውታል።
« ድርድሩ ቢከሽፍ፡ ኤኮዋስ ጦርነት ለመጀመር ጥሩ ምክንያት ያገኛል። ይህ ለምን አይሆንም? »
ፔተር ሂለ/አርያም ተክሌ
መሥፍን መኮንን