ሔልሙት ኮል በ87 ዓመታቸዉ አረፉ።
ዓርብ፣ ሰኔ 9 2009የቀድሞዉ የጀርመን ፌደራል ሪፐብሊክ (ምዕራብ ጀርመን) መራሔ መንግሥት ሔልሙት ኮል ዛሬ አረፉ። 87 ዓመታቸዉ ነበር። እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር ከ1982 እስከ 1998 ድረስ በመራሔ መንግሥትነት ያገለገሉት ሄልሙት ኮል ጀርመን ዳግም እድትዋሐድ በግንባር ቀደምትነት የታገሉ፤ ለዛሬዉ የአዉሮጳ ሕብረት ጥንካሬም ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደረጉ ፖለቲከኛ ነበሩ። ኮል የወግ አጥባቂዉ የክርስቲያናዊ ዴሞክራሲያዊ ሕብረት «CDU» የፖለቲካ ማሕበርን የተቀየጡት ገና በወጣትነታቸዉ ዘመን ነበር። ኮል በቀዝቃዛዉ ጦርነት የመጨረሻ ዘመኖች ወከባ እና ግጭት መሐል ጀርመን ዳግም አዋሕደዉ፤ አዉሮጳን በዘዴ ወደ አዲሱ ዘምን ያሸጋገሩ ብልሕ መሪ ነበሩ። ከሁለተኛዉ የዓለም ጦርነት ወዲሕ ጀርመንን ለረጅም ጊዜ የመሩ ብቸኛዉ ፖለቲከኛም ነበሩ። የሁለት ልጆች አባት ነበሩ። ጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዚግማር ጋብርኤል ሄልሙት ኮል ማረፋቸዉን በሰሙ ጊዜ አንድ ትልቅ ጀርመን ሞተ ሲሉ ነዉ የተናገሩት።
«የቀድሞዉ የጀርመን መራሄ መንግስት ሄልሙት ኮል ከዚህ ዓለም መለየታቸዉን አሁን ሰማን ። የጀርመን ፖለቲከኛ ከፍተኛ ባለሥልጣን ከሁሉ በላይ ደግሞ ታላቅ አዉሮጳዊ ነበሩ። ጀርመን እንድትዋሃድ አዉሮጳ በኅብረት እንድትቆም ከፍተኛ አስተዋፆን ያደረጉ ሰዉ ነበሩ። ይህ ለኛ ትተዉልን ያለፉት ትልቅ ቅርስ ነዉ። በዚህ ሥራቸዉ ሲታወሱ ይኖራሉ። ለቤተሰቦቻቸዉ እና ከልጆቻቸዉ ጋር ይህን ሃዘን እንካፈላለን። እዉነት ነዉ ዛሬ አንድ ትልቅ ጀርመን ሞተ።»
ለሕዝባቸዉ የሚያስቡ ሃገራቸዉን የሚወዱ በመሆናቸዉ ሔልሙት ኮል ይታወሳሉ። ኮል የአንድ ታላቅ ፖለቲከኛ አቋምን ይዘዉ ያገለገሉ ናቸዉ። የመራሔ መንግሥትነት ሥልጣንን ሊይዙ ሲሉ ቃለ መሃላን እንዲህ ሲሉ ነዉ የፈፀሙት።
«በዚህ ታሪካዊ አደባባይ አንድ ነገር ለመናገር ይፈቀድለኝ። አላማዬ እና ግቤ ታሪክ ፍርድዋን ሰታ ለሁለት የተከፈለችዉን እናት ሃገራችንን ጀርመንን መልሶ ማዋሃድና መልሶ አንድ ማድረግ ነዉ።» ሔeልሙት ያለሙት ሞልቶላቸዋል። የበርሊን ግንብ መፍረስ ለፖለቲከኛዉ ለሔልሙት ኮል ከሌሎቹ በልጠዉ በሃገሪቱ ታሪክ ዉስጥ እንዲታዩም ይህ የታሪክ አጋጣሚ እጅግ አድርጎ ረድቶአል። ማደራጀትና ማቀነባበር ዉጤት የሚያመጣም ቋሚ እቅድን ረጋ ብሎ መተለም የሚችሉ ፖለቲከኛ መሆናቸዉን ታሪካቸዉን በመጽሐፍ ያስነበቡት ፀሀፊዎች መስክረዉላቸዋል። በጎርጎረሳዊ 1989ዓ.ም በምስራቅ ጀርመን የሕዝብ እንቅስቃሴ ፈንድቶ የኮሚኒስት አምባገነኖችን ሲያራዉጥ፤ መራሔ መንግሥት ኮልም በዝያዉ ዓመት በዝን ጊዜ የምዕራብ ጀርመን መዲና በሆነችዉ በቦን ከተማ ችግር ዉስጥ ገብተዉ ነበር። በፓርቲያቸዉ በክርስትያን ዴሞክራቶቹ ዉስጥም ሃይለኛ ተቃዉሞ በኮል ላይ ተቀስቅሶ በስልጣን ላይ መዝለቃቸዉ አጠያያቂ ሆኖ ዘልቆ ነበር። በፓርቲያቸዉ ልዩነታቸዉ ሰፍቶ የገዛ ባልደረቦቻቸዉ ከስልጣን ሊaf,ናቅሉዋቸዉ ቻጫፍ ደርሶ ነበር። የሔልሙት ኮልን ታሪክ የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ።
ነጋሽ መሐመድ
ይልማ ኃይለሚካኤል
ሸዋዬ ለገሠ
አዜብ ታደሰ