1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያውያን ተመላሾች በሳውዲ

ዓርብ፣ ሰኔ 9 2009

የምህረት ማብቂያው ጊዜ ከረመዳን ጾም የመጨረሻ ሳምንት ጋር መግጠሙ የሪያድ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ማህበር ሊቀመንበርንም ሆነ የኢትዮጵያ መንግስት የስራ ኃላፊዎችን አሳስቧል፡፡

https://p.dw.com/p/2epq7
Saudi-Arabien Abschiebung illegaler äthiopischer Arbeitsmigranten
ምስል DW/S. Shibru

Ber. Saudi_Zusätzlicher Flug für Riyadh Äthiopische Rückkehrer - MP3-Stereo

የሳዑዲ ዓረቢያ መንግስት ህገወጥ ያላቸውን ኢትዮጵያዊያን ወደ ሀገራቸው እንዲያጓጉዝ ለኢትዮጵያ አየር መንገድ 17 ሳምንታዊ ተጨማሪ በረራዎችን  ፈቀደ፡፡ 
አስር ቀናት ያህል  የቀረው  የምህረት ማብቂያው ጊዜ ከረመዳን ጾም የመጨረሻ ሳምንት ጋር መግጠሙ  የሪያድ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ማህበር ሊቀመንበርንም ሆነ የኢትዮጵያ መንግስት የስራ ኃላፊዎችን አሳስቧል፡፡ የረመዳን የጾም ወር የመጨረሻው ሳምንት በመላው ሳዑዲ ዓረቢያ አብዛኞቹ የመንግስት አገልግሎት መስጫ ተቋማት ዝግ ይሆናሉ፡፡ የሳዑዲ ዓረቢያ መንግስት ህጋዊ የስራ እና የመኖሪያ ፍቃድ ለሌላቸው የውጭ ሀገር ዜጎች የሰጠው የውጡልኝ ቀነ ገደብ ሊጠናቀቅ የቀሩት ከ 10 ብዙም ያልዘለሉ ቀናት ናቸው፡፡ መውጣት የማይፈልጉት ኢትዮጵያዊያን እንዳሉ ሆነው መውጣት የሚፈልጉትም በአይሮፕላን እጦት የተነሳ ቁም ስቅላቸውን እያዩ ነበር፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሳዑዲ መንግስት ተጨማሪ አይሮፕላኖች እንዲያርፉ ፍቃድ ያለመስጠቱ ነበር፡፡ አሁን ግን በሳምንት የ17 ተጨማሪ በረራዎች ፍቃድ መገኘቱ ለኢትዮጵያዊያን ተመላሾችም ሆነ ጉዳዩን በዋናነት ለያዙት ሁሉ ታላቅ እፎይታን ሰጥቷል፡፡ አምባሳደር ጊፍቲ አባሲያ በሳዑዲ አረቢያ ዜጎችን በወጉ ለማስመለስ የተቋቋመው ግብረ ኃይል ሰብሳቢ ናቸው፡፡በሪያድ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ማህበር ሊቀመንበር አቶ ሻወል ጌታሁን እንደሚሉት ደግሞ በአሁኑ ወቅት ወደ ሀገር ለመግባት የሚያስችለውን ሰነድ ፈላጊ ኢትዮጵያዊያን ቁጥር በእጅጉ እየጨመረ ነው ፡፡ መጪው የረመዳን የጾም ወር የመጨረሻው ሳምንት እና ጾሙም ከተፈታ በኋላ የመጀመሪያው ሳምንት የሳዑዲ መንግስት ከፍተኛ የበዓላት ቀን ናቸው በዚህ የተነሳም ዜጎች ከኤምባሲውም ሆነ ከኮሚኒቲው ያገኙትን ያህል አገልግሎት ከሳዑዲዎች ዘንድ ላያገኙ ይችላሉ የሚል ስጋት  እንዳደረባቸው ይገልጻሉ፡፡ ይሁንና በዓዋጁ የመጨረሻ ቀንም ሆነ ከዚያ በሁዋላ ሊከሰቱ ለሚችሉት ሁነቶች በሪያድ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ማህበር እየተዘጋጀ መሆኑን ያብራራሉ፡፡አምባሳደር ጊፍቲ አባሲያ በበኩላቸው በረመዳን ዝግ ምክምያት በሳዑዲ ዓረቢያ በኩል ለሚፈጠሩ መስተጓጎሎችም ሆነ መዘግየቶች ሀላፊነቱ የራሱ የሳዑዲ መንግስት ነው ይላሉ፡፡ከኤምባሲው የጉዞ ሰነድ የወሰዱት እና ወደ ሀገር የገቡትን ቁጥር በማወዳደር የገቡት በጣም ትንሽ ናቸው ያሉት አምባሳደር ጊፍቲ ለዚህም የመጓጓዣሰነድ ከኤምባሲው ወስደው ወደ ስራ መሰማራት ፣ ከሳዑዲ መንግስት በኩልም የመጨረሻውን የመውጫ ሰነድ ከወሰዱ በኋላ ለሀይምኖታዊ ተግባር ወደ ቅዱሳን ቦታዎች ማምራት ብሎም በሳዑዲ የጸጥታ ሀይሎች ቁጥጥር ስር መዋል ሰሞኑን ያጋጠሙ ችግሮች መሆናቸውን አብራርተዋል ፡፡ በሀገር ውስጥ ተመላሾችን ለመርዳትም ሆነ ለማቋቋም ሰሞኑን የተደረጉ ጥረቶችን ያነሱት አምባሳደር ጊፍቲ በተለይ በረመዳን ወር መጨረሻ ሙስሊሞች በዘካቸው እነዚህን ወገኖች እንዲያስቡ ጠይቀዋል፡፡

Saudi-Arabien Abschiebung illegaler äthiopischer Arbeitsmigranten
ምስል DW/S. Shibru

ስለሺ ሽብሩ 

ኂሩት መለሰ

አዜብ ታደሰ