ለህግ ተመራቂዎች የማሻሻያ ፕሮግራም ደንብ በኢትዮጵያ
ዓርብ፣ መጋቢት 9 2008
በኢትዮጵያ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ተግባራዊ መሆን የጀመረው የህግ ማሻሻያ ፕሮግራም ደንብ አላማ የትምህርት ጥራትን ለመጠበቅ ወይም ለማሻሻል ታቅዶ መሆኑን የሚመለከታቸው ባለስልጣናት ያስረዳሉ። ይሁንና በደንቡ አተገባበር ላይ ጥያቄ ያላቸው የህግ ተማሪዎች አልጠፉም።
በቅድሚያ ስለ የህግ ማሻሻያ ደንቡ ምንነት የትምህርት ስትራቴጂ ማዕከል ምክትል ዋና ዲያሬክተር ዶክተር አድማስ ሽብሩ አብራርተውልናል። ይሄው የማሻሻያ ደምብ በተለይ በቀድሞው እና በአዲሱ ፖሊሲ ስር ይገኙ በነበሩ የህግ ተማሪዎች ዘንድ በአተገባበሩ ላይ ጥያቄ አስነስቷል። አንድ ስሙን መጥቀስ ያልፈለገ እና በወላይታ ሶዶ ነዋሪ የሆነ፤ የቀድሞ የህግ ተማሪ በዚሁ ደምብ የተነሳ በተማረው ሙያ መስራት አልቻለም። ስለሆነም ለጊዜው በግል ስራ ነው የሚተዳደረው። ዶክተር ምስጋናው ሰለሞን ፤ግለሰቡ በተማረበት በቅድስት ማርያም ዮንቨርስቲ አካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት ናቸው። ከፍተኛ ተቋሙ በመሸጋገሪያ ፖሊሲው ላይ የነበሩ የህግ ተማሪዎቹን ከ 1999 ዓም በኃላ እና በፊት በሚል ከፋፍሎ እንደሆነ ያስመረቀው ዶ/ር ምስጋናው ይገልፃሉ። ከዚህም በተጨማሪ እንደ ምክትል ፕሬዚዳንቱ የደንቡ ተግባራዊነት የሚወሰነው ተማሪው ትምህርቱን ባጠናቀቀበት ዓመት ሳይሆን በጀመረበት ጊዜ ነው ።
ቅሬታችንን አቅርበን እስካሁን ድረስ ከመንግሥትም ይሁን ካስተማረን ተቋም መፍትሄ ልናገኝ አልቻልንም የሚለው የቀድሞ የህግ ተማሪ ለዶይቸ ቬለ እንደገለፀው በ2004 ዓም ከተማረበት የቅድስት ማርያም ዮንቨርስቲ ተመርቋል።እሱም ምንም እንኳን በ2000 ዓም የህግ ትምህርቱን ቢጀምርም፤ የመልቀቂያ ፈተና እንደማያስፈልገው ተነግሮት ፤ የመጀመሪያው ዲግሪ እንዳገኘ ነው የሚናገረው። የዮንቨርስቲው ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ምስጋናው ግን ይህ በፍፁም ሊሆን አይችልም ይላሉ።
«የመልቀቂያ ፈተናውን መፈተን ካለብንም እድሉ ይመቻችልን» ሲል የጠየቀው የቀድሞ የህግ ተማሪ ጥያቄን በተመለከተ ደግሞ ዶ/ር ምስጋናው ፈተናውን መውሰድ እንደሚችል ነው የነገሩን።
በኢትዮጵያ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ተግባራዊ መሆን የጀመረው የህግ ማሻሻያ ፕሮግራም ደንብ እና ከዛ ጋር ተያይዞ የተጀመረው የመልቀቂያ ፈተናን በተመለከተ ያደረግነውን ሙሉ ዝግጅት በድምፅ ያገኙታል።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሰ