ሄልሙት ሽሚድትና የኢትዮጵያዉያን አስተያየት
ሐሙስ፣ ኅዳር 9 2008
በጀርመንነታቸዉ ብቻ ሳይሆኑ የሚገለፁት በጥሩ አዉሮጳዊነታቸዉ እንደሆነም ይመሰክሩላቸዋል።
የ96 ዓመቱ እዉቅ ፖለቲከኛ የሄልሙት ሽሚድት ዜና ረፍት በጀርመናዉያን ዘንድ በርግጥ ያልተጠበቀ አልነበረም። በብዙኃን መገናኛ ዘዴዎች መታመማቸዉና በርግጥም የጤንነታቸዉ ሁኔታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ ሲዘገብ ነበር የሰነበተዉ። ሶሻል ዲሞክራት ፓርቲ አባል ፖለቲከኛዉ ሄልሙት ሽሚድት ከዚህ ዓለም በሞት እንደተለዩ እንደተሰማ ረፍታቸዉ እንደተሰማ በሀገሪቱ የሚታወቁ ሰዎች የተለያዩ የፖለቲካ ሰዎችን ጨምሮ በርካታ የዓለም መንግሥታትና የመንግሥታት ተጠሪዎች የኃዘን መግለጫን አስተላልፈዋል። በመርቸዲስ ቤንዝ የመኪና አምራች ኩባንያ ዉስጥ የሚያገለግሉትና በጀርመን ሲኖሩ ከሰላሳ ዓመት በላይ የሆናቸዉ፤ ዶክተር ፀጋዬ ደግነህ የእዉቁን ጀርመናዊ የሄልሙት ሽሚድትን ዝና የሰሙት ገና ኢትዮጵያ ሳይለቁ በሕጻንነታቸዉ ነዉ።
ለከፍተኛ ትምህርት በመጡበት በጀርመን ሲኖሩ 47 ዓመታት ተቆጥረዋል ። ጀርመን የመጡት ኬምስትሪ ለማጥናት የነፃ ትምሕርት እድል አግኝተው ነበር ። በዚሁ የትምህርት ዘርፍ በተለይም በኦርጋኒክ ኬምስትሪ እዚሁ ጀርመን የዶክትሬት ዲግሪ አግኝተዋል ።ጀርመናዊዉ ሄልሙት ሽሚድት ታላቅ አዉሮጳዊ ናቸዉ የሚሉዋቸዉ ዶክተር ካህሳይ አስተያየት ሰጥተዉናል።
ወደ ጀርመን ከመጡ ወደ አራባ ሰባተኛ ዓመታቸዉን የያዙትና ባለፈዉ የጎርጎረሳዉያኑ ዓመት 2014 የመጨረሻዉ የአፍሪቃ ንጉስ » በሚል ለጀርመንኛ ቋንቋ አንባብያን አቅርበዉ በቅርቡ ይኸዉ መጽሐፋቸዉን በእንጊሊዘኛ ተተርጉሞ በተለያዩ የአዉሮጳ ሃገራት ከፍተና ተነባቢነትን እንዳገኘ የሚነገርላቸዉ ዶ/ር ልዑል አስፋዉ ወሰን አስራተ ሄልሙት ሽሚድት ጀርመንን ከፈረንሳይ ጋር በማቀራረብ ትልቅ ስራን የሰሩ እዉቅ ጀርመናዊ መሆናቸዉን ይመሰክራሉ።
በርግጥ ዜና ረፍታቸዉ በጀርመናዉያን ዘንድ የሚጠበቅ ጉዳይ ሆኖ ቢቆይም ህዝቡ ሄልሙት ሽሚድት ከዚህ ዓለም ተለዩ የሚለዉን ዜና ሲሰማ እጅግ ማዘኑን በበርሊን ነዋሪ የሆኑት ዶክተር ፀጋዬ ደግነህ ተናግረዋል።
ሄልሙት ሽሚት ከጎርጎረሳዊ 1961 -1965 የሰሜናዊ ጀርመናዊትዋ ከተማ የሃንቡርግ ከተማ ከንቲባ ሳሉ በከተማዋ የደረሰዉን የዉኃ መጥለቅለቅ ተከትሎ የኔቶን ርዳታ ከጠየቁ በኋላ ይላሉ ዶክተር ካሳይ ወልደጊዮርጊስ በጀርመን የአደጋ ዝግጁነት ሕግ ታወጀ፤ የጀርመን ወታደራዊ ኃይልም ለርዳታ እንዲሳተፍ ተደነገገ።
ስመጥሩና በተምሳሌትነት የሚቀርቡት ጀርመናዊዉ ሄልሙት ሽሚድት በአዉሮጳ አንድነት ብሎም የጋራ መገበያያ ገንዘብ ለመመሥርት መሠረት እንደሆኑም ዶክተር ካሳይ ወልደጊዮርጊስ ይናገራሉ። ዶክተር ካሳይ ወልደጊዮርጊስ ሄልሙት ሽሚድት በጋዜጣ አዘጋጅነት መሳተፋቸዉን ገልፀዋል። ዶ/ር ልዑል አስፋዉ ወሰን አስራተም በጋዜጣ አዘጋጅነታቸዉ መታወቃቸዉን ገልፀዉልናል።
ሄልሙት ሽሚድት በትዳራቸዉ ወደ ሰባ ዓመት ከሚወዱዋቸዉ ባለቤታቸዉ ከሎኪ ሽሚድት ጋር ኖረዉ ሁለት ልጆችን አፍርተዋል። ሎኪ ሽሚድት ግን የዛሬ አምስት ዓመት ነበር ባለቤታቸዉን ሄልሙት ሽሚድትን የተለዩዋቸዉ።
አዜብ ታደሰ
አርያም ተክሌ