ሁለተኛ ዙር የኮሮና ወርሽኝ ስጋት በጀርመን
ዓርብ፣ ሐምሌ 24 2012
ጀርመንና የተለያዩ የአዉሮጳ ሃገራት በየሃገራቸዉ ላይ ሁለተኛ ዙር የኮሮና ወረርሽኝ ስርጭት እንዳይነሳ ስጋት አሳድሮአል። ዘጠኝ አጎራባች ሃገራት ያላት ጀርመን ለበጋ እረፍት በመኪና ዉጪ ሐገር ሰንብተዉ ወደ ጀርመን የሚመለሱ ነዋሪዎች ሁሉ የኮሮና ምርመራ እንዲያደርጉ የሚጠይቅ ደንብ እንዲወጣ እያለች ነዉ። የባቫርያ ግዛት ጠቅላይ ሚኒስትር ማርኩስ ሶደር ኮሮና ተኅዋሲ ስርጭትን ለመግታት በሚደረግ ጥረት ባቀረቡት ሃሳብ በጀርመን የሚኖሩ ዜጎች ከዉጭ ሲመለሱ ምርመራ ሊደረግላቸዉ የሚገባዉ በአዉሮፕላን ጣብያዎች ብቻ ሳይሆን በድንበር በኩል ወደ ሃገሪትዋ በተሽከርካሪ የሚገቡትም ጭምር መሆን አለበት ብለዋል። የሰሜኑ ንፍቀ-ክበብ የበጋ የዕረፍት ጊዜ ዉጪ ሐገር ሰንበተዉ የሚመለሱ የጀርመን ነዋሪዎች ሲመለሱ ተሕዋሲዉን ያዛምታሉ ተብሎ ተፈርቶአል። ጠቅላይ ሚኒስትር ማርኩስ ሶደር እንደተናገሩት በቫርያ ግዛት ወደ ዉጭ የሚወጡ እና ከዉጭ ለሚገቡ ተጓዦች የመኪና አዉራ ጎዳናዎች ላይ የኮሮና ምርመራ እናደርጋለን፤ በባቫርያዎቹ ሙኒክ እና በኑረንበርግ ከተሞች የኮረና ማዕከል ይከፈታል ብለዋል። ከዚህ ሌላ በባቡር ጣብያዎች ተጓዦች ላይ የኮሮና ምርመራ እናካሂዳለንም ብለዋል። ለእረፍትም ሆነ ለሌላ ጉዳይ ዉጭ ቆይተዉ የሚመጡ የጀርመን ነዋሪዎች ኮሮና ተኅዋሲን ላለማሰራጨት በራስ ፈቃደኝነት ለ 14 ቀናት ራሳቸዉን አግልለዉ በራሳቸዉ ቤት መቆየታቸዉ በቂ አይደለም ያሉት ሶደር፤ ወደ ጀርመን ተመላሽ የዉጭ ሃገር ተጓዥ ሁሉ የኮሮና ምርመራ እንዲያደርጉ ደንብ መዉጣት አለበት ሲሉ ተናግረዋል። ጀርመንን ጨምሮ የተለያዩ የምዕራብ ሃገራት ለኮሮና በሽታ ፍቱን ነዉ የተባለ ክትባት ሙከራላይ እንደሆኑ ቢናገሩም እስካሁን ግን ለመከላከያ ተብሎ ግን ጥቅም ላይ አልዋለም።
አዜብ ታደሰ
ይልማ ኃይለሚካኤል