የዩጋንዳ ምርጫና የሰብዓዊ መብት ጥሰት
ዓርብ፣ ጥር 7 2013የዩጋንዳ ሕዝብ የወደፊት መሪዉን ለመምረጥ ትናንት ድምፅ ሲሰጥ ነዉ የዋለዉ። በወጣቱ ድምፃዊ-ፖለቲከኛ ቦብ ዋይን ከፍተኛ ፉክክር የገጠማቸዉ የ 76 ዓመቱ ፕሬዝደንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ምርጫዉን አሸንፊያለሁ እያሉ ነዉ። ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቬኒ ዘንድሮ ለ6ኛ ዘመነ-ሥልጣን ነዉ የተወዳደሩት። የ76 ዓመቱ አዛዉንት ሥልጣን ከመያዛቸዉ በፊት በጦርነትና ግጭት የተመሰቃቀለችዉን ዩጋንዳን በማረጋጋታቸዉ በተለይ በሐገሪቱ ገጠራማ አካባቢዎች በሚኖረዉ ሕዝብ ዘንድ ከፍተኛ ድጋፍ ያገኛሉ ተብሎ ይገመታል። እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ እንደ ቅርብ አጋርና ወዳጅ የሚደግፋቸዉ ምዕራቡ ዓለም ግን ሙሴቪኒን ገሸሽ እያደረጋቸዉ ነዉ። ትናንት በተካሄደዉ ምርጫ ከሁለቱ ሌላ 9 ፖለቲከኞች ለፕሬዝደንትነት ይፎካከራሉ። 45 ሚሊዮን ከሚገመተዉ የዩጋንዳ ሕዝብ ከ17 ሚሊዮን የሚበልጠዉ ለምርጫ ተመዝግቧል። በዩጋንዳ ቀደም ሲል የምረጡኝ ዘመቻ በሚካሄድበት ወቅት በርካታ ጋዜጠኞች ታስረዋል፤ ፖለቲከኞች ተደብድበዋል፤ ተገድለዋልም። ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪዉ ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽናል በሰዎች ላይ የሚካሄድ ክትትል እስራት እና ግድያ በአስቸኳይ እንዲቆም ሲል ጠይቆአል። በዩጋንዳ ምርቻዉን ተከትሎ ያለዉን ነገር ዓለማቀፉ ማኅበረሰብ እንዲከታተል ሲል የዓለሙ የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪ ድርጅት ጠይቆአል።
ይልማ ኃይለሚካኤል
አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ