የኮሮና ክትባት በጀርመኑ የመድሐኒት አምራች
ሰኞ፣ ጥር 24 2013የጀርመኑ ባየር የመድሐኒት አምራች ኩባንያ በመጭዉ ዓመት 160 ሚሊዮን ክትባትን እንደሚያመርት ይፋ አደረገ። ባየር የመድሐኒት አምራቹ ድርጅት እንዳስታወቀዉ፤ ድርጅቱ በአሁኑ ወቅት ለኮሮና መከላከያ ይሆናል ብሎ ሊያመርት ያቀደዉን ክትባት በ 36 ሺህ ሰዎች ላይ ሙከራ እያደረገ ነዉ። የጀርመኑ የመድሐኒት ኩባንያ ባየር የመጀመርያዉ የኮሮና መከላከያ ክትባትን በያዝነዉ የጎርጎረሳዉያን 2021 ዓመት መጨረሻ ይፋ እንደሚያደርግ ጨምሮ አስታዉቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ አስትራዜኒካ በመባል የሚታወቀዉ የክትባት አምራች ኩባንያ ተጨማሪ የኮሮና መላከያ ክትባትን ለአዉሮጳ ኅብረት እንደሚቀርብ አስታወቀ። የክትባት አምራች ድርጅቱ አቀርበዋለሁ ያለዉ ይህ ክትባት ለአዉሮጳ ሃገራት አቀርበዋለዉ ካለዉ በተጨማሪ እንደሆነ ኅብረቱ ዛሬ አስታዉቋል። የአዉሮጳ ኅብረት ኮሚሽን ፕሬዚዳንት ኦርዙላ ፎን ደር ላይን ዛሬ በትዊተር ገፃቸዉ እንዳስነበቡት፤ የክትባት አምራቹ ድርጅት አስታራዜኒካ፤ ለኅብረቱ እለከዋለሁ ካለዉ 80 ሚሊዮን ክትባት ተጨማሪ በሚቀጥሉት ወራቶች 40 ሚሊዮን ክትባቶችን ለኅብረቱ ያቀርባል። አስትራዜኒካ ክትባቱን የሚያቀርበዉ ለኅብረቱ አቀርባለሁ ብሎም ከሰጠዉ ቀነቀጠሮ አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ነዉም ተብሎአል። ባለፈዉ ሳምንት የክትባት አምራቹ ድርጅት የኮሮና ክትባትን በማቅረብ ረገድ በመጀመርያና ቀጣይ ብሎ በሰጠዉ መረሃ-ግብር ላይ የአዉሮጳ ኅብረት እና ብሪታንያን ሲወዛገቡ እንደነበር አይዘነጋም።
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ