1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኮሌራ በሽታን ከኢትዮጵያ ለማጥፋት የተያዘው እቅድ

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 17 2015

በጎርጎሪዮሳዊው የዘመን ቀመር 2028 ዓም የኬሌራ ወረርሽኝን ከኢትዮጵያ ለማጥፋት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስትሯ ዶ/ር ሊያ ታደሰ እንዳሉት ለስምንት ዓመታት በተያዘ እቅድ መሠረት ደግሞ በኮሌራ የሚከሰተውን የሞት ምጣኔ በ90 በመቶ ዝቅ ለማድርግ ተወጥኗል።

https://p.dw.com/p/4LR2G
Äthiopien PK Gesundheitsminiterin Liya Tadese und Energieminister Asfaw Dingamo
ምስል Seyoum Getu/DW

የጤና ሚኒስቴር መግለጫ

 

የጤና ሚኒስትር ዶ/ር ሊያ ታደሰ ከባለፈው ነሐሴ ወር ጀምሮ የኮሌራ ወረርሽኝ በሶማሊ ክልል መከሰቱን፤ እስካሁንም በኦሮሚያ ክልል ሁለት ዞኖች እና በሶማሊ ክልል አንድ ዞን 11 ወረዳዎችን ማዳረሱን ገልጸዋል። ሚኒስትሯ « እስከ ተያዘው ታኅሣስ ወርም 696 ሰዎች ላይ በሽታው ተከስቶ 24 ሰዎች በዚሁ ምክንያት አልፈዋል።» ብለዋልም። በባለፉት አራት ወራት በኦሮሚያ ባሌ እና ጉጂ ዞኖች 9 ወረዳዎች እንዲሁም በሶማሌ ክልል ሊበን ዞን ሁለት ወረዳዎች በሽታው በወረርሽኝ መልክ ተነስቶ ተደርጓል ባሉት ርብርብ አሁን ላይ መቆጣጠር መቻሉንም አመልክተዋል።

ባለፉት ጥቂት ዓመታት በተለይም ከአምስት ዓመታት በፊት በሽታው በመላው አገሪቱ በስፋት ይከሰት እንደነበር ያመለከቱት ዶ/ር ሊያ ከሦስት ዓመታት ወዲህ ግን የበሽታውን ስርጭት በመግታት የሞት ምጣኔውንም 30 በመቶ በመቀነስ ወደ 3 በመቶ ዝቅ ማድረግ መቻሉን አብራርተዋል። በተለይም በጎርጎሪዮሳዊው 2017 ወደ 47 ሺህ ሰዎች በበሽታው ተይዘው እንደነበር፤ የዛሬ ሦስት ዓመት ገደማ የኮሌራ ክትባትም ጭምር በሽታው በተከሰተባቸው አካባቢ በመስጠት፤ ስፋቱን መቀነስ መቻሉንም ተናግረዋል። የኮሌራና ኮሮና መከላከያ ክትባት በጋምቤላ

ሀሬና ቡሉቅ፣ ደሎ መና፣ በርበሬ፣ መዳ ወላቡ፣ ጉራ ዳሞሌ፣ ቀርሳ ዱላ፣ ጊርጃ እና ጎሮ በሁለቱ ክልሎች በሽታው በዚህ ዓመት ከተከሰተባቸው አከባቢዎች ተብለው ተጠቅሰዋል። የበሽታውን ስርጭት በመቆጣጠር ረገድ የውኃ እና መስኖ ሚኒስቴር የባለድርሻ ሚናን ከተጫወቱ መካከል ናቸው ተብሏል። አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ በውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የውኃና ሳኒቴሽን ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ናቸው። «በባሌ ዞን ሦስት ወረዳዎች ማለትም ሀሬና ቡሉቅ፣ ደሎ መና እና በርበሬ ወረዳዎች ወረርሽኙ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲከሰት የውኃ ማከሚያ በማቆም ንጹህ የመጠጥ ውኃ ተደራሽ በማድረግ ወረርሽኙን በእነዚህ አከባቢ መግታት ተችሏል። ሌሎች ወረርሽኙ በተከሰተባቸው ወረዳዎችም ንጹህ ውኃን በተቻለ መጠን ተደራሽ በማድረግ ችግሩን ለመቅረፍ ጥረት ተደርጓል።» ብለዋል።የኮሌራ መከላከያ ክትባት በደቡብ ኢትዮጵያ

ኮሌራ አሁንም ኢትዮጵያ ውስጥ በተደጋጋሚ የሚከሰት በሽታ ሆኗል። እንደ ጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር ሊያ ታደሰ ማብራሪያ ይህንኑን ከግንዛቤ ውስጥ በማስገባት በ2028 በሽታውን ሙሉ በሙሉ ከኢትዮጵያ ለማጥፋት እቅድ ተነድፏል። ለቀጣይ ስምንት ዓመታትም የትግበራ መርሃግብር ተወጥቷል።

«ይህ የስምንት ዓመት የባለድርሻ አካላቱ እቅድ የወረርሽኙን የሞት ምጣኔ በ90 በመቶ ዝቅ የማድረግ እቅድ አለው። በዚህ መሠረት በአገር አቀፍ ደረጃ ኮሌራ የሚከሰትባቸው 118 ወረዳዎች ተለይቶ የመጠጥ ውኃ አቅርቦት እና ንጽህናን በማሻሻል በሽታው ሲከሰትም በቂ ህክምና እንዲያገኙ በማስቻል ነው በሽታውን ለመቆጣጠር የታቀደው። በእነዚህ ወረዳዎች ወደ 16 ሚሊየን ህዝብ ይኖርባቸዋል። «እስከ 2025 15.5 ሚሊየን ህዝብ ለመከተብም ታቅዷል» ነው ያሉት ሚኒስትሯ።

ሥዩም ጌቱ 

ሸዋዬ ለገሠ

እሸቴ በቀለ