የኦሮምያ ብልጽግና ፓርቲ አመራሮች መታገድ
ሰኞ፣ ነሐሴ 4 2012የኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ ለሁለት ቀናት ባካሄደው ጉባኤ የፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልና የመከላከያ ሚኒስትር አቶ ለማ መገርሳንና ሁለት ሌሎች የፓርቲውን የበላይ አመራሮች ማገዱ ልዩ ልዩ አስተያየቶች እየተሰጡበት ነው።ፓርቲው ትናንት ማምሻውን እንዳስታወቀው አቶ ለማ መገርሳ፣ዶክተር ሚልኬሳ ሚዴጋንና ወይዘሮ ጠይብ ሀሰንን ከፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልነት በጊዜያዊነት አግዷል።ዶክተር ሚልኬሳ የኦሮምያ ብልጽግና ፓርቲ ፅህፈት ቤት ሃላፊ አማካሪ ፣ ወይዘሮ ጠይብ ሀሰን ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ናቸው።የፖለቲካ ሳይንስ ምሁርና የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ በምህጻሩ (ኦፌኮ) ሊቀመንበር ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ስለ ፓርቲው ውሳኔ ለዶቼቨሌ በሰጡት አስተያየት ልዩነቱ አስቀድሞም የሚታወቅ ቢሆንም ውሳኔው ግን ለብልጽግና ፓርቲ ይጠቅማል የሚል እምነት እንደሌላቸው ተናግረዋል። ልዩነቱም በእርቅ ቢፈታ የተሻለ እንደሚሆን መክረዋል።የህግ ባለሙያ እና ጠበቃ ወንዲሙ ኢብሳ በበኩላቸው ክስተቱ ፣ ህዝቡ ወደፊትም ከግለሰቦች ይልቅ በተቋም ጥንካሬ ላይ ተስፋ እንዲያደርግ የሚያሳስብ ነው ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባው ወኪላችን ስዩም ጌቱ ጉባኤው ስላሳለፈውን የእገዳ ውሳኔና በእገዳው ላይ የተሰጡ አስተያየቶችን ያካተተ ዘገባ አጠናቅሯል።
ስዩም ጌቱ
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ