1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ሳይንስ

የኢንተርኔት ዋጋ እናንተንም ያሳስባችኋል?

ዓርብ፣ መጋቢት 14 2010

#77ከመቶው የተሰኘው የዛሬው የወጣቶች ዓለም ዝግጅት ትኩረት የአፍሪቃ የኢንተርኔት አገልግሎትን ይመለከታል። ከሌላው የዓለማችን ክፍል ጋር ሲነፃፀር ኢንተርኔት አፍሪቃ ውስጥ ብዙም አልተስፋፋም፣ ዋጋዉም ውድ የሚባል ነው። ኢንተርኔት መጠቀም የድሎት ወይስ ፍፁም ከህይወታችን ሊጎል የማይገባ? ዶይቸ ቬለ አጠያይቋል።

https://p.dw.com/p/2ucC4
Symbolbild Stress Kopfschmerzen
ምስል Colourbox/Wodicka

በዚህ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ኢንተርኔት የኑሮዋችን አንዱ አካል እየሆነ መጥቷል። በአጭር ቅፅበት ውስጥ ሌላ ሀገር ካለ ሰው ጋር በቀላሉ መልዕክት እንድንለዋወጥ እድል ከፍቶልናል። ሌሎች ናይጄሪያ መዲና አቡጃ የሚገኙ ወጣት ተሟጋቾች ደግሞ ኢንተርኔትን ፖለቲካ እና ማህበራዊ ግንዛቤን ለማስጨበጥ ይጠቀሙበታል። እንዴት? የዶይቸ ቬለዋ ካትሪን ጌንዝለር ወጣቶቹን ጠይቃለች።
ሀምዛት ላዋል ናይጄሪያ ውስጥ ስሙ ይታወቃል። የ 25 ዓመቱ ወጣት  ሁለት ስልኮቹን እና ላፕቶፑን በተደጋጋሚ ቶሎ ቶሎ ይመለከታል። ያለ ኢንተርኔት ዛሬ  ህይወት ለእሱ የማትታሰብ ናት። «  አዎ! ለመጀመሪያ ጊዜ ኢንተርኔት ስጠቀም እንዴት እንደነበር አስታውሳለሁ። በወቅቱ አስማት ነበር የመሰለኝ። አስገራሚ ነበር። የፈለኩትን ጉግል ማድረግ እችል ነበር»

followthemoney ናይጄሪያ የተሰኘው ድርጅት መስራች ሀምዛት ዛሬ ሰባቱንም ቀናት ለ24 ሰዓታት ኢንተርኔት ይጠቀማል። « አንዳንድ ሰዎች ህይወትህ ኢንተርኔት ላይ ነው ይሉኛል። ሁልጊዜ ትዊተር እና ፌስ ቡክ ውስጥ ነኝ። የተለያዩ ድረ ገፆችን እጎበኛለሁ። እንዲሁም ኢንተርኔት በመጠቀም የማህበረሰቦችን ድምጽ ለማጉላት እሞክራለሁ። ስለዚህ ይህ በጣም አጓጊ እና የሚያበረታታ ነው። በዓለም ዙሪያ ካሉ በመቶ ሚሊዮን ከሚቆጠሩ ወጣቶች ጋር ትስስር አለኝ። ሀሳቦችን ሲለዋወጡ፣ እውቀትን ሲለዋወጡ፣ መረጃን ሲያጋሩ  ሌሎችንም ያነቃቃሉ። » ሀምዛት እና ባልደረቦቹ ናይጄሪያ ውስጥ እየተዘዋወሩ ቦታዎችን ይጎበኛሉ። በኋላም በጉዞ ላይ የገጠማቸውን ድረ ገፃቸው ላይ፣ በትዊተር እና ፌስ ቡክ ለሰፊው ማህበረሰብ ያጋራሉ። በገፃቸውም አማካኝነት ከማህበረሰቡ እና ፖለቲከኞች ጋር ይገናኛሉ። 

Äthiopien Addis Abeba Universität Kommunikation Internetsperre
ብዙዎች ኢትዮጵያ ውስጥ የኢንተርኔት አገልግሎት በስልካቸው ስለማያገኙ Wifi ያለበት ቦታ እየሄዱ ይጠቀማሉ ምስል DW/J. Jeffrey

እንደ ናይጄሪያ የኮሚኒኬሽን ኮሚሽን ከሆነ 91 ሚሊዮን የሚሆነው የናይጄሪያ ህዝብ የኢንተርኔት ተጠቃሚ ነው። ይህም ሰፊ ገበያ እና በኢንተርኔት አቅራቢ ኩባንያዎች መካከል ከፍተኛ ፉክክር እንዲኖር ረድቷል። ላለፉት አምስት ዓመታት የአገልግሎቱ ዋጋ ከአሁኑ በሶስት እና አራት እጥፍ የጨመረ ነበር። ዛሬ 10 GB የኢንተርኔት ዳታ 14 ዩ ኤስ ዶላር ገደማ ይሸጣል። አይቮሪ ኮስት ውስጥ ይህ ዋጋ በእጥፍ ይጨምራል። ቤኒን የ 1 GB ዋጋ 5 ዶላር ነው። የበለጠ ዳታ በገዙ ቁጥር ዋጋው በመጠኑም ቢሆን ይቀንሳል። ይሁንና በርካታ ናይጄሪያውያን በአገልግሎቱ ደስተኛ አይደሉም። ለምሳሌ በሹፍርና ስራ ተሰማርቶ የሚገኘው ሳኒ አባ። ኢንተርኔት በመጠቀም ጊዜ ማሳለፍ ደስ ነው የሚለው። « በቀን ከሶስት ሰዓት ያነሰ እጠቀማለሁ። ለሳምንት 150 ሜጋ ባይት እንገዛለን። አገልግሎቱን የሚሰጡት ያ ለሳምንት ይበቃል ይላሉ። ግን ዳውን ሎድ ካደረግን ወይም ዩ ቱዩብ ከተጠቀምን ዳታው ቶሎ ነው የሚያልቀው።» 

ሌላው ፈተና የአገልግሎቱ ጥራት ነው። እንደ አቡጃ ያሉ አካባቢዎች ጥራቱ የተሻለ የሚባል ነው። ወደ ገጠሩ አካባቢ የተኬደ እንደሆነ ግን ተጠቃሚዎች ይማረራሉ። ለዚህም ሳኒ አባ የራሱ የሆነ መፍትሄ ፈጥሯል።« አምስት መስመሮች አሉኝ። ሁለቱ ለኔ ወሳኝ ናቸው። ብዙ መስመር የምጠቀመው የኢንተርኔት አገልግሎቱ ጥሩ ስላልሆነ ነው። »

ናይጄሪያ ውስጥ ኢንተርኔት በተሻለ መልኩ የሚሰራው ዘመናዊዎቹ ስልኮች ለሚጠቀሙት ነው። ያለ ገመድ እቤት ውስጥ ኢንተርኔት የሚጠቀሙት ባለሀብቶች እና መስሪያ ቤቶች ብቻ ናቸው። ከወጪው ባሻገር ደግሞ የኤሌክትሪክ አገልግሎት በተደጋጋሚ ስለሚቋረጥ ኢንተርኔትም ይቆራረጣል። በትናንሽ ከተሞች ሰዎች ወደ ኢንተርኔት ካፌ መሄዱን ይመርጣሉ። ሳሚዬ ሚካኤል ሀገሩ አንድ ቀን እንደ ሌሎች ሃገራት ነፃ አገልግሎት የሚሰጡ ቦታዎችን ታስፋፋለች ብሎ ተስፋ ያደርጋል። « እያንዳንዱ WIFI የሚስጥር ቁልፍ አለው። ሌሎች የላቁ ሃገራት ግን ለምሳሌ ትናንት ለንደን ካለች ኋደኛዬ ጋር ሳወራ ነበር። WIFI እንዴት እንደሚሰራ ስትገልፅልኝ ነበር። ይሄ ከአቅማችን በላይ አይደለም። ተሟጋቹ ሀምዛት ላዋላ በተመጣጣኝ ዋጋ የሚቀርብ የኢንተርኔት አገልግሎት የናይጄሪያን ማህበረሰብ በበጎ ይቀይረዋል ብሎ ያምናል። 


የኢንተርኔት አገልግሎት ዋጋ እናንተንም እንደነዚህ ደቡብ አፍሪቃውያን አበሳጭቷችሁ ይሆን? 

 


ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ቡርኪና ፋሶ እና ጋቦን ከአፍሪቃ የኢንተርኔት አገልግሎታቸው መጥፎ ከሚባሉት ሃገራት ተርታ ይሰለፋሉ። እንደ ኬንያ ሞሮኮ እና ደቡብ አፍሪቃ ያሉት ደግሞ ብዙም ኋላ ቀር የሚባሉ አይደሉም። ይሁንና  በዝግጅታን መግቢያ ላይ እንደሰማችሁት በርካታ የደቡብ አፍሪቃ ወጣቶች የዋጋው ነገር ያበሳጫቸዋል። የመክፈል አቅም ጉዳይም ተጠቃሚውን እየለያየው ይገኛል። ዘጋቢያችን ስቴፋን ሞል ወጣት ደቡብ አፍሪቃውያንን አነጋግሮ ነበር። 
ቮዳኮም 21 ሚሊዮን ደንበኞች ያሉት የደቡብ አፍሪቃ ኩባንያ ነው። ጆሀንስበርግ ውስጥ ያለ ሰማይ ጠቀስ ፎቁን ግን ብዙዎች በደስታ ሳይሆን በብስጭት ነው የሚመለከቱት። ምክንያቱም ግብፅ እና ናይጄሪያ ውስጥ 1 GB የኢንተርኔት አገልግሎት ወደ 33 ብር ገደማ በሚሸጥበት ወቅት ሁለት ትላልቅ የደቡብ አፍሪቃ ኩባንያዎች ኤም ቲ ኤን እና ቮዳኮም ተጠቃሚዎቻቸውን 10 እጥፍ ያህል ስለሚጠይቁ ነው። የደቡብ አፍሪቃን ያህል አይሁን እንጂ ኢትዮ ቴሌኮምም ቢሆን ለ 1GB 165 ብር ይጠይቃል።  የደቡብ አፍሪቃ ግማሽ ያህል ማህበረሰብ ደግሞ ዋጋው ከአቅሙ በላይ ነው። ተማሪ እስቴሲ ቁጣዋን ትገልፃለች። «በጣም ውድ ነው።  ከሌሎች የአፍሪቃ ሃገራት ጋር ብናነፃፅረው እንኳን ዋጋው የዚህን ግማሽ ነው። ይህ ነው የሚያናድደኝ። ቮዳኮም ደቡብ አፍሪቃ ውስጥ ከሆነ ለምንድን ነው በሌሎች ሀገራት የሚረክሰው? የሌላውንም ህዝብ ሂሳብ ነው እንዴ እየከፈልን ያለነው? በአሁኑ ሰዓት ይህ ነው የሚያበሳጨኝ። ፍፁም ተቀባይነት የሌለው ነገር ነው።»
ሁሴን ደግሞ « እንደ IT ባለሙያ አሁን የተሻለ የኢንተርኔትን መገናኛ የት እንዳለ መፈተሽ አለብኝ። የምጠቀመው የዳታ መጠን በተሻለ መልኩ እንዲሆን። በጣም ደካማ ነው!
#DataMustFall የሚሉ የማህበራዊ መገናኛ ዘመቻዎች በሀገሪቱ ተጠቃሚ ላይ ያለውን የዋጋ ጫና በማንፀባረቅ ትኩረት ስበዋል። ብዙዎችም የሚወያዩበት ርዕስ ሆኗል። በጆሀንስበርግ ሜትሮ ኤፍ ኤም ስቱዲዮ ስለዚሁ ጉዳይ ለመወያየት ጋዜጠኛው ወጣቶችን ጋብዘዋል።
አትሞ 
#DataMustFall ስለሚለው ዘመቻ ወጣቶቹ የሚያውቁትን እየጠየቀ ጋዜጠኛው ይወያያል። 
የኢንተርኔት ዳታ በሚገዛዉ መጠን ዋጋዉ ይቀንሳል፤ ይህም ማለት ትንሽ GB ዋጋዉ ከትልቁ ይወደዳል። ያ ማለት ደግሞ ወጣቶች እና  ብዙ ገንዘብ የሌለው ደሀው ማህበረሰብ የበለጠ እንዲከፍል ይገደዳል ማለት ነው። ደሀ ተማሪዎች በኢንተርኔት አማካኝነት የመማር ዕድላቸውን እያጡ ነው ትላለች የነርስነት ተማሪዋ ምፎ ሞፋከኝ።«ከሌሎች የኢንተርኔት አገልግሎት ካላቸው ልጆች ጋር ሳነፃፅረው ከእኔ የበለጠ ብዙ ያውቃሉ።»

Bildergalerie Johannesburg Stadt zwischen Verfall und Wiederauferstehung
ቮዳኮም 21 ሚሊዮን ደንበኞች ያሉት የደቡብ አፍሪቃ ኩባንያ ነውምስል DW/T. Hasel

« እነዚህ እንዲመረቁ የምንፈልጋቸው ጥቂት ተማሪዎች ናቸው። እንዳያጠኑ መሰናክል ከገጠማቸው ለእነሱ አግባብ አይደለም። ምናልባትም የአፍሪቃ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ለኢንተርኔት መብት ሊታገሉ  ይገባል። ምናልባትም እንደ ውኃ እና ዳቦ ወይም ምግብ መካተት አለበት።»ይላል። ጋዜጠኛ አካ DJ ዞላ
ለኢንተርኔት መብት የምትሟገተው ክሊዮፓትራ ሴዚ ለአመታት የተሻለ የኢንተርኔት አቅርቦት እንዲኖር ታግለን ነበር ትላለች። « የኢንተርኔት ዳታ የምቾት አይደለም። ግንኙነት የመፍጠር መብት አለን። በአሁኑ ሰዓት ግን ይህ ሲሆን አልመለከትም ምክንያቱም ይህንን ዳታ መግዛት የሚችሉት ቢሮዋቸው ወይም ሥራ እና ቤታቸው ኢንተርኔት ያላቸው ሰዎች ናቸው። እነሱ ብቻ ናቸው በነፃ መገናኘት የቻሉት።  ደሀውስ? ሥራ የሌለውስ የሰው ኃይል? ይህ ነው ትልቁ ጥያቄ።»
ኢንተርኔት ለብዙዎች የተሻለ ህይወት በር ከፋች ሆኗል። ይህ በር ግን ለበርካታ አፍሪቃውያን አሁንም ዝግ ሆኖ ይቆያል። አፍሪቃውያን ወጣቶች እየተወያዩ ለአፍሪቃ የተሻለ ቅርፅ እንዲሰጡ ዕድል በሚከፍተው #77ከመቶው የወጣቶች ዓለም ዝግጅታችን እናንተም ተካፈሉ ምን ቢደረግ ይህ ችግር ሊቀረፍ ይችላል ትላላችሁ?  
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሰ