የኢትዮጵያ ምርጫ ግንቦት 28 አይካሔድም
ቅዳሜ፣ ግንቦት 7 2013ማስታወቂያ
ከ20 ቀናት ገደማ በኋላ ሊካሔድ ቀነ-ቀጠሮ የተያዘለት የኢትዮጵያ አገራዊ ምርጫ ሊራዘም እንደሚችል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ። በአንድ ሳምንት ልዩነት ይካሔዳል የተባለው የአዲስ አበባ እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች ምርጫም አገራዊው በሚደረግበት ዕለት እንዲሆን ተወስኗል።
የኢትዮጵያ አገራዊ ምርጫ ግንቦት 28 ቀን 2013 ዓ.ም. ሊካሔድ ተቀጥሮ ነበር። የምርጫው ዕለት መቀየሩ ይፋ የሆነው በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ባደረገው ውይይት ነው።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ "ግንቦት 28 ቀን የድምጽ መስጠት እና ቆጠራውን አጠናቀን ምርጫውን መከወን እንደማንችል ተረድተናል" ሲሉ ተናግረዋል።
በውይይቱ በመራጮች ምዝገባ ወቅት ገጥመዋል የተባሉ ችግሮች ዋንኛ የመወያያ አጀንዳ ሆነው ነበር።
የመራጮች ምዝገባ ትናንት ግንቦት 6 ቀን 2013 ዓ.ም. ተጠናቋል። እስካሁን ድረስ የመራጮች ምዝገባ ከ36 ሚሊዮን በላይ መራጮች ተመዝግበዋል። ይኸም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ይመዘገባሉ ብሎ ከጠበቀው 78 በመቶ ገደማ መሆኑ ተገልጿል።
ዮሐንስ ገብረእግዚዓብሔር
እሸቴ በቀለ
ታምራት ዲንሳ