1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአፋር ነፃ አውጪ ግንባር ጥያቄ

ሐሙስ፣ መስከረም 22 2012

የአፋርና ሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች ተደጋጋሚ ግጭቶች የተስተዋሉባቸው ሥፍራዎች ናቸው። በነዚህ አካባቢዎች በየጊዜው ለሚነሱ ግጭቶች መንግሥት ዘላቂውን መፍትሄ እንዲሰጥ የአፋር ነፃ አውጪ ግንባር ጠይቋል።

https://p.dw.com/p/3QhCe
Äthiopien Landschaft in Provinz Afar Kamele durch die Wüste
ምስል picture-alliance/dpa

መንግሥት ዘላቂውን መፍትሄ እንዲሰጥ ጠይቀዋል

በአፋርና ሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች በየጊዜው ለሚነሱ ግጭቶች መንግሥት ዘላቂውን መፍትሄ እንዲሰጥ የአፋር ነፃ አውጪ ግንባር ጠየቀ፡፡ በአርብቶ አደሩ ዘንድ የሚፈጠሩ ችግሮችን በመፍታት ረገድ የመከላከያ ሠራዊት ከወገንተኝነት የፀዳ ሥራ ሊሰራ ይገባል ብሏል፡፡ የአፋር ነፃ አውጪ ግንባር ፓረቲ ፀሐፊ አቶ ሀንፍሬ መሀመድ ለDW በስልክ እንደገለፁት በአርብቶ አደሩ ኅብረተሰብ ዘንድ የሚፈጠሩ ችግሮችን የፀጥታ ኃይሉ ከወገንተኝነት በፀዳ መልኩ መፍታት ይገባል፡፡ ከቀናት በፊት በአካባቢው ችግሩን ለማረጋጋገት በፀጥታ ኃይሉ የተወሰደው እርምጃ አግባብ አለመሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የፓርቲው አመራር በሁለቱ አርብቶ አደር ክልል ጎሳዎች መካከል በየጊዜው የሚነሳው ግጭት ዘላቂ መፍትሄ ሳያገኝ ረዥም ዓመታት ቆይቶበታል ያሉትን ምክንያትም ተናግረዋል። ሁልጌዜ የሚካሄድ ተመሳሳይ ግጭት ኅብረተሰቡ ተገቢውን የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በማንሳት መፍትሄ እንዳይጠይቅ እና ለውጥ እንዳይመጣ የሚያደርግ በመሆኑ ፓርቲው  ዘላቂ መፍትሄ ያስፈልገዋል ብሎ እንደሚያምን ተናግረዋል። አቶ ሀንፍሬ አሁንም መንግሥት ኅብረተሰቡን ማወያየትና ዘላቂ መፍትሄ ማምጣት አለበት ብለዋል። በአፋርና የሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች መካከል ሰሞኑን ተቀስቅሶ በነበረ ግጭት የሰው ሕይወት ማለፉንና ከዚሁ ጋር በተያያዘ በተለይ በአፋር ክልል በኩል እርምጃ ተወስዷል በሚል የተሰሙ መረጃዎችን አስመልክቶ ለማረጋገጥ ወደ አፋር ክልል ኮሚዩኒኬሽን በተደጋጋሚ ብንደውልም ምላሽ ማግኘት አልቻልንም።


መሳይ ተክሉ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
አዜብ ታደሰ