1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ተሿሚ ሚኒስትሮቹ ቃለ መሀላ ፈጽሙ

ረቡዕ፣ መስከረም 26 2014

ሦስቱ ሚኒስትሮች ከብልጽግና ፓርቲ ውጭ ናቸው።ዶክተር ብርሃኑ ነጋ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ ፓርቲ ኢዜማ መሪ፣ አቶ በለጠ ሞላ ጌታሁን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ አብን  ሊቀመንበር እንዲሁም አቶ ቀጀላ መርዳሳ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ኦነግ ምክትል ሊቀመንበር ናቸው። ተሿሚ ሚኒስትሮቹም ዛሬ በምክር ቤቱ ቃለ መሀላ ፈጽመዋል።

https://p.dw.com/p/41M4g
Der neue Ministerrat von Äthiopien
ምስል House of people’s representative of Ethiopia

የኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ዛሬ ባካሄደው በ6ኛ ዙር 1ኛ አመት 1ኛ ልዩ ስብሰባው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ያቀረቡትን የአዲሱን መንግሥት 22 የሚኒስትሮች ምክር ቤት አባላት ሹመት አጽድቋል። ሹመቱ የጸደቀው በሁለት ተቃውሞና በ12 ድምጸ ተዐቅቦና በአብላጫ ድምጽ ነው። ከመካከላቸው ሦስቱ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ባለሥልጣናት ናቸው። ተሿሚ ሚኒስትሮቹም ዛሬ በምክር ቤቱ ቃለ መሀላ ፈጽመዋል ። ምክር ቤቱ ሹመታቸውን አጽድቆላቸው ቃለ መሀላ የፈጸሙት የአዲሱ ካቢኔ አባላት   
1. አቶ ደመቀ መኮንን የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር
2. ዶ/ር አብርሃም በላይ የሀገር መከላከያ ሚኒስትር
3. አቶ አህመድ ሽዴ የገንዘብ ሚኒስትር
4. ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል የስራና ክህሎት ሚኒስትር
5. አቶ ኡመር ሁሴን የግብርና ሚኒስትር
6. ኢንጅነር አይሻ መሃመድ የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር
7. ዶ/ር ኢንጀነር ሃብታሙ ኢተፋ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር
8. ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ቦንገር የትምህርት ሚኒስትር
9. ወ/ሮ ዳግማዊት ሞገስ- የትራንስፖርትና ሎጀስቲክ ሚኒስትር
10. አቶ ገ/መስቀል ጫላ የንግድና እና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር
11. አቶ መላኩ አለበል የኢንደስትሪ ሚኒስትር
12. አቶ ብናልፍ አንዱዓለም አሸናፊ የሰላም ሚኒስትር
13. ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ የፍትህ ሚኒስትር
14. ዶ/ር ሊያ ታደሰ የጤና ሚኒስትር
15. አቶ በለጠ ሞላ ጌታሁን- የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር 
16. አምባሳደር ናኒሴ ጫሌ- የቱሪዝም ሚኒስትር
17. አቶ ላቀ አያሌው- የገቢዎች ሚኒስትር
18. ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ ኢብራሂም-የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር
19. ታከለ ኡማ በንቲ- የማዕድን ሚኒስትር
20. ዶ/ር ፍፁም አሰፋ- የፕላን ልማት ሚኒስትር
21. ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ-የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር
22. ቀጀላ መርዳሳ -የባህልና ስፖርት ሚኒስትር
ናቸው። 
ከመካከላቸው ሦስቱ ከብልጽግና ፓርቲ ውጭ ሲሆኑ እነርሱም ዶክተር ብርሃኑ ነጋ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ ፓርቲ ኢዜማ መሪ፣ አቶ በለጠ ሞላ ጌታሁን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ አብን  ሊቀመንበር እንዲሁም አቶ ቀጀላ መርዳሳ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ኦነግ ምክትል ሊቀመንበር ናቸው። ምክር ቤቱ የሚኒስትሮቹን ሹመት ከመቀበሉ በፊት የፌዴራል መንግስት የአስፈፃሚ አካላት ሥልጣንና ተግባርን መወሰኛ ረቂቅ አዋጅን አጽድቋል።22 ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን ያካተተው አዲሱ የኢትዮጵያ መንግሥት መዋቅር ከዚህ ቀደም በአዋጅና በሌሎች ይመሩ የነበሩ 32 ተቋማትም የታጠፉበት ነው። በሰላም ሚኒስቴር ሥር የነበሩ እና ሌሎች ዋና ዋና የተባሉ 20 መስሪያ ቤቶች በጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ሥር እንዲሆኑ መደረጉንም የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ለኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባደረጉት ገለጻ አስረድተዋል። መስሪያ ቤቶቹን ለመምራት የተሾሙት የ22 ሚኒስትሮች ምርጫ የትውልድ አካባቢን፣ ጾታን፣ የሥራ ልምድን፣ ብቃትን፣ የሃይማኖት ስብጥር እና የማገልገል ፍላጎትን መሰረት ያደረገ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እጩ ሚኒስትሮቹን ለምክር ቤቱ ባቀረቡበት ወቅት አስታውቀዋል። ተልዕኳቸውም «በዋናነት ሌብነትንና ልመናን ማጥፋት የሁሉም ኢትዮጵያዊ አገልጋይ»መሆን እንዲሆን ያሳወቁት ዐቢይ ይህን አቅደው የሚሰሩ ካቢኔ እንዲሆኑም ጠይቀዋል። በአዲሱ የመንግሥት አወቃቀር  ለተካተቱት ለተፎካካሪ ፓርቲ አመራር የካቢኔ አባላትም «ተቋም መምራት እና ተቋም መቃወም የተለያዩ መሆናቸውን» እንዲረዱ በማስገንዘብ «በጋራ መስራት እንደምንችል የምናሳይበት ምህዳር እንዲሆን እጠይቃለሁ»ብለዋል።ለብልጽግና አመራሮችም«ልባችንን እና ጭንቅላታችንን ክፍት አድርገን ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከተሾሙት ጋር በትብብር መንፈስ መስራት አለብን» በማለት  አሳስበዋል፡፡ዶቼቬለ ያነጋገራቸውበአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎች የካቢኔ አባላቱ ስብጥር መልካም ጅምር ነው ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል። ከአስተያየት ሰጭዎቹ መካከል አንዳንድ ምደባዎች የትምህርት ዳራን ያላማከሉ ናቸው ያሉም ይገኙበታል።