1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአውሮጳ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ

ዓርብ፣ ጥር 26 2009

በትንሽዋ ደሴት ማልታ ዋና ከተማ ቫሌታ ዛሬ የተጀመረው የአውሮጳ ህብረት አባል ሀገራት የመሪዎች ጉባኤ ከአፍሪቃ ወደ አውሮጳ የሚደረግ ህገ ወጥ ስደትን ለመግታት ያስችላሉ ያላቸውን አዳዲስ እርምጃዎች አፀደቀ ። ከመካከላቸው ሰው አሻጋሪዎችን ለመቆጣጠር በተመድ ለሚደገፈው የሊቢያ መንግሥት እገዛ ማድረግ ይገኝበታል ።

https://p.dw.com/p/2Wx70
EU-Gipfel auf Malta | Gruppenbild
ምስል Getty Images/AFP/A. Solaro

M M T/ EU -Gipfel Migration - MP3-Stereo

ዛሬ ጠዋት የተጀመረው የዚህ ጉባኤ ዋነኛ ትኩረት የህብረቱ የወደፊት አቅጣጫ ፣የስደተኞች ጉዳይ  እና የህብረቱ ፕሬዝዳንት ለአውሮፓ ህብረት ስጋት  ያሏቸው አዲሱ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ናቸው ። የህብረቱ አባል ሀገራት ዛሬ በጉባኤያቸው ያስቀደሙት ግን የስደተኞችን ጉዳይ ነበር ። ቀጣዩ ዘገባ ህብረቱ ህገ ወጥ የሚላቸው ስደተኞች እንዳይመጡበት እስካሁን የወሰዳቸውን እን ለወደፊቱም ያሰባቸውን እርምጃዎች ይመለከታል ። 

«የአውሮፓ ህብረት ፍፁም አይደለም ፤ሆኖም ፈተናዎቻችንን ለመወጣት ሊያገለግለን የሚችል የተሻለ መሣሪያ እንጂ» ሲሉ ነበር ባለፈው መስከረም ብራቲስላቫ ስሎቬክያ ውስጥ የተሰበሰቡት የአውሮጳ ህብረት መሪዎች ጉባኤያቸውን ሲፈጽሙ ያሳወቁት ። መሪዎቹ ይህን ያሉት የብሪታንያ ህዝብ ከአውሮጳ ህብረት ለመውጣት ከወሰነ በኋላ ባካሄዱት የመጀመሪያ ጉባኤያቸው ላይ ነበር ። ዛሬ በቅድሚያ የተወያዩት ግን አውሮጳ እስካሁን አንድ የጋራ መፍትሄ ማግኘት ባቃተው በስደተኞች ጉዳይ ላይ ነው ። በአውሮጳ ህብረት ምክር ቤት የክርስቲያን ሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ  ቡድን መሪ ማንፍሬድ ቬበር ችግሩ ሊፈታ ያልቻለው አባል ሀገራት ቃላቸውን መጠበቅ ባለመቻላቸው ነው ይላሉ።
«ማልታ የስደተኞችን ጉዳይ አንስቶ ለመወያየት እና የመጨረሻ መፍትሄ ለማግኘት ተመራጭ ሀገር ናት ። አባል ሀገራቱ ባለፉት ዓመታት ያወጧቸውን ህጎች በስተመጨረሻ ተግባራዊ እንዲያደርጉ ነው የምመኘው ። በቫሌታ ለምሳሌ እስካሁን 40 በመቶው ብቻ የተሳካው የስደተኞችን ፍልሰት ለመግታት የታቀደው ለአፍሪቃ የሚሰጠው እርዳታ ውሳኔ ያገኛል ። አባል ሀገራት ብዙ ቃል ቢገቡም በተግባር አይተረጉሙትም ።ይህ ለወደፊቱ መቀጠል የለበትም ።»
ከጎርጎሮሳዊው 2015 አንስቶ ስደተኞች ወደ ህብረቱ አባል ሀገራት በብዛት መግባት ከጀመሩ በኋላ ህብረቱ ስደተኞችን ለመግታት ልዩ ልዩ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ ነው ። የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ህገ ወጥ የሚሉትን  ስደት ለመቆጣጠር የተጠናከረ የድንበር ቁጥጥር ተግባራዊ አድርገዋል ። የስደተኞች መነሻ እና መተላለፊያ ከሆኑ አንዳንድ የአፍሪቃ ሀገራት ጋር የስደት ምንጭን ማድረቅ ያስችላሉ የተባሉ እርምጃዎችንም በመውሰድ ላይ ናቸው ። ከዚህ ሌላ ህብረቱ የስደተኞች መተላለፊያ ከሆነችው የአውሮፓ ህብረት ጎረቤት ቱርክ ጋር ስደተኞችን በሀገርዋ እንድታቆይ ውል ፈርሟል ። ባለፉት ዓመታት ኢጣልያ እና ግሪክ የገቡ ስደተኞችን እና ተገን ጠያቂዎችን አባል ሀገራት እንዲከፋፈሉ ህብረቱ ያቀረበው ሀሳብ ከተወሰኑ አባል ሀገራት በስተቀር አብዛኛዎቹ ተግባራዊ አላደረጉትም ። በዚህ የተነሳም አሁን  አማራጭ ከተባሉት መፍትሄዎች ውስጥ ከባህር ላይ ለሚታደጓቸው ስደተኞች በሰሜን አፍሪቃ ማቆያ ካምፕ መገንባት አንዱ ነው ። በህብረቱ የመካከለኛ ጊዜ ግብ መሠረት በሜዴትራንያን ባህር አድርገው ወደ አውሮጳ ለመግባት የሚሞክሩ ስደተኞችን ከታደጉ በኋላ እንደ እስካሁኑ ወደ ኢጣልያ ከመውሰድ ይልቅ ሰሜን አፍሪቃ ለመመለስ ነው የታሰበው ። ይህንኑም የአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ባለፈው ሳምንት አረጋግጠዋል ።በአውሮፓ ህብረት ምክር ቤት የሶሻል ዴሞክራቶቹ ፓርቲ ተወካይ ጆ ላይነን ህብረቱ በሜዴትራንያን ባህር በኩል አውሮጳ ለመግባት የሚሞክሩ ስደተኞች መነሻ ከሆነችው  ከሊቢያ ጋር ትብብሩን ቢያጠናክር ነው የሚበጀው ይላሉ ። 
«እንደሚመስለኝ አስቸጋሪ ቢሆንም የአውሮፓ ህብረት ከሊቢያ ባለሥልጣናት ፣ ከማናቸውም ጋር ቢሆን መደራደር አለበት ። የሊቢያ የባህር ጠረፍንም በንቃት መጠበቅ ይኖርብን ይሆናል ። የደህንነት አገልግሎት ሰጭዎች ስላሉን ምን እንደሚከናወን ማየት ይቻላል ።እዚያ ምን እንደሚደረግ የሚታዘቡም አሉ ።ስለዚህ ከስደተኞቹ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ የሚወስዱትን ሰው አሻጋሪዎች ማስቆም ይቻላል ።»
ከመሪዎቹ ጉባኤ አንድ ቀን አስቀድሞ ሊብያ የሚገኙ  ሰው አሻጋሪዎችን ለማደን እና ለመከላከል ኢጣልያ እና ሊቢያ በቅርብ ትብብር ለመሥራት ተስማምተዋል ። 

EU-Gipfel auf Malta | Gruppenbild
ምስል Reuters/Y. Herman
Mittelmeer Rettung von Flüchtlingen
ምስል picture alliance/AP Photo/E. Morenatti

 

ኂሩት መለሰ

ገበያው ንጉሴ

ነጋሽ መሐመድ