የተመች ወረርሽኝ ሥጋት በኢትዮጵያ ስድስት ክልሎች
ዓርብ፣ ሰኔ 3 2014በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተከሰተውን የተምች ወረርሽኝ ለመከላከል ርብርብ እየተደረገ እንደሚገኝ የፌደራል ግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ ፡፡ የሚኒስቴሩ አንድ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊ ዛሬ ለዶቼ ቬለ DW እንደገለጹት በስድስት ክልሎች የተከሰተውን ወረርሽኝ ለመከላከል የፀረ ተባይ ኬሚካልና የመርጫ መሣሪያዎች አቅርቦትን ጨምሮ በቅንጅት እየተሠራ ይገኛል፡፡ የመከላከል ሥራው ሰብል አብቃይ በሆኑ አካባቢዎች በወረርሽኙ ምክንያት ሊያጋጥም የሚችለውን የምርት መቀነስ ለማስቀረት ያስችላል ተብሏል፡፡
በኢትዮጵያ በአብዛኞቹ አካባቢዎች የተከሰተው የተምች ወረርሽኝ ወትሮም እንደነገሩ በሆነው የአገሪቱ የግብርና ምርት ላይ ስጋት መደቀኑ አልቀረም፡፡ መነሻውን ደቡባዊውን የኢትዮጵያ ክፍል ያደረገው ወረርሽኝ በቡቃያ ላይ የሚገኙ ሰብሎችንና በግጦሽ ሳሮች ላይ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል የሚል ሥጋት እንዳደረባቸው በተለይ በደቡብና በሲዳማ ክልል የሚገኙ አርሶ አደሮች እየገለፁ ይገኛሉ፡፡
በፌዴራል ግብርና ሚኒስቴር የእጽዋት ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ በላይነህ ንጉሴ አሁን ባለው ሁኔታ የተምች ወረርሽኙ በስድስት ክልሎች ውስጥ መታየቱን ነው ለዶቼ ቬሌ DW የገለፁት ፡፡ ወረርሽኙ የከፋ ጉዳት ሳያስከትል በቁጥጥር ሥር ለማዋል አስቀድሞ ዝግጅት መደረጉን የሚናገሩት አቶ በላይነህ ለዚህም ለክልሎች የፀረ ተባይ ኬሚካልና የመርጫ መሳሪያዎች ሥርጭት ተደርጓል ብለዋል፡፡
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ