1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የቤተ-ክርስትያን ቃጠሎ በሀገረ ሠላም   

ማክሰኞ፣ ሐምሌ 16 2011

"በሲዳማ ሀገረ ሠላም አካባቢ የሚገኙት ዶያ ሚካኤል፣ ገሳባ ገብረክርስቶስ እና ጭሮኔ አማኑኤል የተባሉት ሦስት አብያተ ክርስትያናት ላይ ቃጠሎ ደርሷል። አብያተ ክርስትያናቱ እንዳይቃጠሉ ሲከላከሉ ከነበሩ ምዕመናን መካከልም የሞቱ ይሁንና ይህን መረጃ በእርግጠኝነት ለማጣራት ቦታዉ ላይ መሄድ ይጠበቅብናል"

https://p.dw.com/p/3MYVq
Ghana Atewa Forest | Kyebi Forest Reserve
ምስል Getty Images/AFP/C. Aldehuela

ለአንድ ሳምንት የሚቆይ የፀሎት መርሃ-ግብር ተጠርቶአል

በደቡብ ክልል ሲዳማ ዞን በሀገረ ሠላም የሚገኙ ሦስት አብያተ-ክርስትያናት መቃጠላቸዉን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን የሲዳማ፣ የጌዶ፣ አማሮ እና ቡርጂ ሃገረ ስብከት ቢሮ አስታወቀ። በሲዳማ ሀገረ ሠላም አካባቢ የሚገኙት ዶያ ሚካኤል፣ ገሳባ-ገብረክርስቶስ እና ጭሮ አማኑኤል የተባሉት ሦስት አብያተ ክርስትያናት መቃጠላቸዉን የሃገረ ስብከቱ ምክትል ስራ አስኪያጁ መጋቢ ሐይማኖት ቀሲስ ነፃነት አክሎግ ለዶይቼ ቬለ «DW» ዛሬ ገልፀዋል። በተለያዩ አብያተ ክርስትያናት ላይ የተሰነዘረውን ጥቃት ለመከላከል ምዕመናን ከፍተኛ ርብርብ ማድረጋቸዉን የተናገሩት የሃይማኖት አባት፤ በርካታ ዲያቆናት ከአካባቢዉ ሸሽተዉ በኦሮሚያ ክልል ቤተ-ክርስትያን ተጠልለዋል ብለዋል።  
በአሁኑ ሰዓት ግን የመረጋጋቱ ሁኔታ በመሻሻሉ፤ የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ ነገ ስፍራዉ ላይ ተገኝቶ ሁኔታዉን ለማጣራት ቀጠሮ መያዙን መረጃ ደርሶኛል ሲሉ አስረድተዋል።  የሃገረ ስብከቱ ሊቀ-ጳጳስ አካባቢዉ ላይ የሚገኙ አብያተ ክርስትያናት ለአንድ ሳምንት የሚቆይ የፀሎት መርሃ-ግብር እንዲደረግ አዝዘዉ ከትናንት ጀምሮ ምህላ መጀመሩን ተናግረዋል። አዜብ ታደሰ መጋቢ ሐይማኖት ቀሲስ ነፃነት አክሎግን አነጋግራቸዋለች። 

አዜብ ታደሰ 
ተስፋለም ወልደየስ