1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሳዑዲ ለሴቶች ክልክል የነበሩ መብቶችን እየፈቀደች ነው

ሰኞ፣ ጥር 7 2010

የሳዑዲ ሴቶች በሀገሪቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ባለፈው አርብ ጥር 4 ቀን 2010 ዓ.ም በጅዳ በሚገኝ ስቴድየም ተገኝተው የእግር ኳስ ጨዋታ ለመመልከት በቅተዋል፡፡ በቀጣዩ ቀን በዋና ከተማይቱ ሪያድ የሚገኝ ስቴድየምም ሴት ተመልካቾችን አስተናግዷል፡፡

https://p.dw.com/p/2qsES
Frauen Stadion Saudi Arabien
ምስል Getty Images/AFP

ሳዑዲ ለሴቶች ክልክል የነበሩ መብቶችን እየፈቀደች ነው

የሳውዲ መንግስት በጎርጎሮሳዊው 2018 የመጀመሪያ ሳምንታት በመላ ሀገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች ይተገበራሉ ካላቸው መብቶች አንዱ የሆነው ሴቶች በኳስ መጫዎቻ ሜዳዎች ገብተው ኳስ የመመልከት መብት ሲሆን ይህም ባሳለፍነው አርብ ጥር 4 ቀን 2010 ዓ.ም. በይፋ ተጀምሯል። በጅዳ የንጉስ አብደላ የስፖርት ማዘውተሪያ አል ጁሃራ ኳስ ሜዳ በሳዑዲ ታዋቂ የእግር ኳስ ክለቦች በአል አህሊ እና በአል ባጥል የተደረገውን ጫወታ የሳዑዲ ሴቶች ከቤተሰቦቻቸው ጋር በመሆን ለመጀመሪያ ጊዜ በተዘጋጀላቸው ቦታ ሆነው ጨዋታውን ታድመዋል።

የሳዑዲ ሴቶች የዜግነት መብታቸው ከወንዶች እኩል ይከበር ዘንድ ከፍተኛውን ትጋት ካሳዩት የሀገሪቱ መሪዎች መካከል የሳዑዲው ንጉስ አብደላ በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ። የሀገሪቱ ሴቶች በተለያዩ ትላልቅና ትናንሽ ኩባንያዎች፣ በመንግስት መዋቅር በሚተዳደሩ መስሪያ ቤቶች፣ በማዘጋጃ ቤት ምክር ቤት፣ በሃገሪቱ ከፍተኛ ህግ አውጭና አስፈጻሚ አካል በአልሹሁራ ምክር ቤትን ጨምሮ እስከ ሚኒስቴር ማዕረግ ሴቶች ተሳታፊ እንዲሆኑ ንጉስ አብደላ ፈር ቀዳጅ እርምጃ ማድጋቸው ይጠቀሳል።

የንጉስ አብደላን ህልፈት ተከትሎ በትረ ስልጣኑን የተረከቡት ወንድማቸው ንጉስ ሰልማን ቢን አብድልአዚዝ በወንድማቸው የተጀመረውን የሴቶች መብትን የማስጠበቅ በተሃድሶ አጠናክረው ቀጥለውበታል። ንጉስ ሰልማን ከመጀመሪያ የስልጣን ዘመናቸው ጀምሮ የሴቶች መብት ሙሉ በሙሉ እንዲከበር ተደጋጋሚ አዋጆችና መመሪያዎችንም ማውጣታቸው የሚታወስ ነው።

Frauen Stadion Saudi Arabien
ምስል Getty Images/AFP

የሴቶችን መብት ለማክበር ቁርጠኛ አቋም የያዙት ንጉስ ሰልማን የአልጋ ወራሽነቱን ስልጣን ለጎልማሳው ልጃቸው ለልዑል መሀመድ ሰልማን ካስረከቡ በኋላ ደግሞ የወጡትን አዋጆችና መመሪያዎች ተከትሎ በማስፈጸሙ ረገድ አልጋ ወራሽ መሀመድ አመርቂ የሚባሉ እርምጃዎች በመውሰድ ላይ ናቸው። አልጋ ወራሽ ልዑል መሀመድ ሳዑዲን ከነዳጅ መር ኢኮኖሚ ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለማስኬድ ከወጠኑት የ2030 እቅድ መሳ ለመሳ የእስልምናን ሀይማኖት ወግና ባህል በማይጻረር መልኩ ሀገራቸውን በማዘመን የዜጎች በተለይም የሴቶችን መብት እንደሚያስከብሩ ደጋግመው አሳውቀዋል። አልጋ ወራሹ የሴቶች መኪና የመንዳት ጥያቄ አይነት አወዛጋቢ እና አነጋጋሪ ሆነው የቆዩ የመብት ጥያቄዎችን ለማክበር ጠበቅ ያለ እርምጃ በመውሰድ ላይ ናቸው።

የሴቶች መኪና የመንዳት መብት በያዝነው አመት አጋማሽ ሐምሌ ወር ገደማ እንደሚፈቀድ በይፋ ቀን ቆርጠው አሳውቀዋል። ከዚሁ ጋር የሳዑዲ ሴቶች ተከልክለው የባጁበት የሀይማኖት ትምህርት (ፈትዋ) የመስጠት ፈቃድ፣ ለግማሽ ክፍለ ዘመን ዝግ የነበረው ፊልሞችን በሲኒማ ቤት መመልከት፣ ሴቶች በስፖርት ማዘውተሪያ ቦታዎች የመሳተፍና የመታደምን መብት ጨምሮ ተዛማጅ የሆኑ መብቶች ይከበሩ ዘንድ ውሳኔ ላይ ተደርሷል። ይህ መብት የማክበር ጉልህ ውሳኔ ሳዑዲ ለያዘችው የ2030 የተሃድሶ እቅድ ሴቶች ለሀገራቸው እድገት ቁልፍ ሚና እንዲጫወቱ እድል ከፋች አንደሚሆን የሀገሪቱ አስተዳዳሪና ዘዋሪ አልጋ ወራሽ መሀመድና አባታቸው ንጉስ ሰልማን ደጋግመው አስታውቀዋል።
 

ነቢዩ ሲራክ

ተስፋለም ወልደየስ

አርያም ተክሌ