የሜርክል፤ ፓርቲዉን በማገልገሌ ለኔ ትልቅ ክብር ነዉ
ዓርብ፣ ኅዳር 28 2011የጀርመኑ የክርስቲያን ዴሞክራቶች ህብረት ፓርቲ በምህጻሩ «CDU» ዛሬ በጀመረው ጉባዔ ለ18 ዓመታት ፓርቲውን የመሩትን መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክልን የሚተካ ሊቀመንበር ይመርጣል ተብሎ እየተጠበቀ ነው። በሰሜን ጀርመንዋ በሀምቡርግ ከተማ በሚካሂደው በዚሁ ጉባኤ መክፈቻ ላይ ሜርክል የመሰናበቻ ንግግር ለማድረግ ወደ መድረኩ ሲወጡ እና ንግግራቸውንም ሲጨርሱም ጉባኤተኞቹ ለረዥም ደቂቃዎች በመቆም አድናቆታቸውን እና ምስጋናቸውን በጭብጨባ ገልጸውላቸዋል። ላለፉት 13 ዓመታት ጀርመንን የመሩት የ64 ዓመትዋ ሜርክል የመሀል ቀኙን ፓርቲያቸውን «የክርስቲያን ዴሞክራቶች ህብረት» በፍጥነት ወደ ፖለቲካው ማዕከል ማምጣት በመቻላቸው ይደነቃሉ። መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ከፓርቲ ሊቀመንበርነታቸዉ እንደሚለቁ የተናገሩት ባለፈው ጥቅምት ውስጥ ነበር። ሜርክል ገና 3 ዓመት የሚቀረዉን የመራሒተ መንግሥት ስልጣናቸዉን እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል። የሜርክልን መንበር ለመያዝ በመፎካከር ላይ ያሉት የፓርቲው ዋና ፀሀፊ የ56 ዓመትዋ አነግሬት ክራምፕ ካረንባወር ፣ የቀድሞው የፓርቲው የምክር ቤት ተጠሪ የ63 ዓመቱ ፍሪድሪሽ ሜርትስ እና የአሁኑ የጤና ሚኒስትር የ38 ዓመቱ የንስ ስፓን ናቸው። የሜርክል ምርጫ ክራምፕ ካረንባወር ናቸዉ። የበርሊኑ ወኪላችን ይልማ ኃይለሚካኤል የአንጌላ ሜርክል ወራሽ በሚል የመራሒተ መንግሥትዋን የፖለቲካ ጉዞ የሚያስቃኝ ዘገባ ልኮልናል።
ይልማ ኃይለሚካኤል
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ