ውይይት፦ ኢትዮጵያ እና የስራ አስፈፃሚው አካላት አወቃቀር የሕግ ረቂቅ
እሑድ፣ ጥቅምት 4 2011ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የኢህአዴግን ሙሉ ድጋፍ በማግኘት ለሁለተኛ ጊዜ በሊቀመንበርነት ከተመረጡ በኋላ በመጀመሪያ ይወስዷቸዋል ተብለው ከሚጠበቂት ርምጃዎች መካከል አንዱ በአስፈጻሚ አካላት አደረጃጀት ላይ ያደርጉታል የሚባለው ለውጥ ነው። በዚሁ መሰረትም የመንግሥት የሚንስትሮች ምክር ቤት ሰሞኑን ባካሄደው ስብሰባ የላዕላይ አስፈጻሚ አካላትን መልሶ ለማዋቀር የሚያስችለውን ረቂቅ ሕግ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መላኩ ተገልጿል።
የኢትዮጵያ ሚኒስትሮች ምክር ቤት የአገሪቱን ስራ አስፈፃሚ አወቃቀር ለመከለስ ባቀረበው ረቂቅ ሕግ መሰረት፣ የሚንስቴር መስሪያ ቤቶች ቁጥር አሁን ካለው 28 ወደ 20 ዝቅ ይላል፣ አዲስ የሚዋቀሩ መኖራቸውም ተጠቁመዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መንግሥታቸው የአስፈፃሚ አካላትን እና ተቋማትን ቁጥር ለመቀነስ የወሰነው በወጪ ምክንያት መሆኑን ሲያስታውቁ፣ ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ ደግሞ "በዜጎች ተዓማኒነት ያላቸው ተቋማት እንዲኖሩና ያሉትም እንዲጠናከሩ" እየተሰራ መሆኑን ሁለቱን ምክር ቤቶች ባለፈው ሰኞ በከፈቱበት ጊዜ ተናግረው ነበር።
የፌደራል አስፈጻሚ አካላት አወቃቀር ማሻሻያ ተቋማቱን ፈጥኖ ውጤታማ የመሆን ችሎታ ያላቸው ተቋማት ማድረግ ያስችላል? ብዙዎች ተቋማቱ የተጣለባቸውን ኃላፊነት በመወጣቱ ረገድ ውጤታማ ናቸውን? ውጤታማ እንዲሆኑ ምን ሊደረግ ይገባል? በእነዚህ ጥያቄዎች ላይ የፖለቲካ ተንታኞችን እና አንድ ባለሙያ አወያይተናል።
አርያም ተክሌ
ልደት አበበ