ዉለታና መልሱ
ማክሰኞ፣ መስከረም 17 2015እንደ አብዛኞቹ በዓላት ሁሉ የመስቀል በዓል ዘንድሮ ሲከበሩም በዓሉን አክባሪዎች ለሰላም እንዲፀልዩ፤ አቅመ ደካሞችን በጣሙን በጦርነት የተጎዱ ወገኖቻቸዉን እንዲረዱም የኃይማኖቱ መሪዎች ይመክራሉ። የባሕርዳሩ ወኪላችን ዓለም ነዉ መኮንን የአንድ ተፈናቃይን የትናንትንና የዛሬ ሕይወየትን ከአንድ በጎ አድራጊ ቸርነት ጋር አሰባጥሮ ይተርክልናል። የመረዳዳትና የዉለታ መላሽነት እሴት ብሎታል ርዕሱን።
ሀብታሙ ደምሴ ነዋሪነቱ ዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ሰቆጣ ከተማ ሲሆን ባለፈው ዓመት በአካባቢው በነበረው ጦርነት ምክንያት 5 ቤተሰቦቹን ይዞ ወደ ባህር ዳር ተፈናቅሎ ነበር፣ ባህርዳር ሲደርስ ግን እንደሌሎች ተፈናቃዮች በካምፕ አልተቀመጠም ይልቁንም አቶ አሞኘ መንግስቴ የተባሉ ነዋሪ አንድ ክፍል በነፃ ሰጥተውት አካባቢው ከጦርነት ነፃ እስኪሆን እንደኖረና ከዚይም ሰቆጣ በመንግስት ቁጥጥር ስር ስትሆን ወደ ትውልድ ቦታው እንደተመሰ ለዶይቼ ቬሌ ተናግሯል፡፡ ሀብታሙ በወቅቱ አስጠግተውት የነበሩትን አባወራ በስማቸው ከመጥራት ይልቅ አብርሀም ይላቸዋል፣ ለምን ስንል ጠይቀነው ነበር። እንደ ሀብታሙ “በክርስትና እምነት አብርሀም ቤቱን ለእንግዶች የተወ ደግ አባት ነበር” በማለት አስረድቷል፡፡
ሌሎች ጎረቤቶቹም እንደወንድምና እህት ይቆጥሩትና የቻሉትን ያህል እገዛ ያደርጉለት እንደነበር ሀብታሙ ያስረዳል፡፡ አቶ ባምላኩ አይተነው የተባሉ ሌላው ጎረቤትም ማነኛውንም የሚያስፈልግኝን ነገር እንድጠቀም ሲፈቅድልኝ ሙሉሰው መብራት የተባሉ ነዋሪና ባለቤቱ ደግሞ ከቤታቸው እንድገባ ከነበርኩበት ቤት አስፈቅደው ወስደው አኑረውኛል ሲል ነው ሀብታሙ የተናገረው፡፡
ባለፈው የመስቀል በኣል ዝግጅት “አገሬ ሰላም ሆኖ ወደ ሰቆጣ ከተመለስኩ ተመልሼ መጥቼ የመስቀልን በዓል አብሬ እውላለሁ” ባለው መሰረት ረጅም ጉዞ አቋርጦ ባህር ዳር ፍየልና ሌሎች ለበዓሉ ዝግጅት የሚያስፈልጉ የሚያስፈልጉ ነገሮችን ገዝቶ መምጣቱን ቤት በነፃ ሰጥተውት የነበሩት አቶ አሞኘ መንግስቴ ይገልፃሉ፡፡
ሀብታሙ ደምሴ ቃል በገባው መሰረት የዘንድሮውን መስቀል በዓል ከሰቆጣ በመነሳት ወንዝና ተራራ ሸለቆና አቀበት አቋርጦ በችግር ወቅት ከደረሱለት ሰዎችና ረቤቶቻ ጋር ባህርዳር እያከበረ ነው፡፡
ዓለምነው መኮንን
ነጋሽ መሐመድ
ታምራት ዲንሳ