ካታሎንያን ለመገንጠል የሚንቀሳቀሱ የስፔን ፖለቲከኞች እስር ተፈረደባቸው
ሰኞ፣ ጥቅምት 3 2012ማስታወቂያ
የስፔን ከፍተኛ ፍርድ ቤት የካታሎንያን መገንጠል የሚያቀነቅኑ ፖለቲከኞች ከዘጠኝ እስከ 13 ዓመታት እንዲታሰሩ በየነ። ሕዝብን በመንግሥት ላይ መነሣሣት ወንጀል ተከሰው ጉዳያቸውን ሲከታተሉ የነበሩት ዘጠኙ ተጠርጣሪዎች ዛሬ የተፈረደባቸው በመላ ግዛቲቱ ተቃውሞ በቀሰቀሰው እና ካታሎንያን ከስፔን ለመገንጠል በተደረገው እንቅስቃሴ በነበራቸው ሚና ጥፋተኛ በመባላቸው ነው። በጎርጎሮሳዊው ጥቅምት 2017 ዓ.ም. በስፔን መንግሥት የተከለከለ ሕዝበ-ውሳኔ ተካሒዶ የካታሎንያ ግዛት ለአጭር ጊዜም ቢሆን ሉዓላዊነቷን ስታውጅ እጃቸው አለበት የተባሉ ሌሎች ሦስት ተጠርጣሪዎች «በአለመታዘዝ» ጥፋተኛ ሆነው ቢገኙም እስር ሳይበየንባቸው ቀርቷል። ሁሉም ተጠርጣሪዎች በተከሰሱበት የአመጽ ወንጀል ነፃ ቢባሉም የፍርድ ቤቱን ውሳኔ አምርረው ተቃውመዋል። እስር የተበየነባቸው ፖለቲከኞች የካታሎንያ ሰዎች ተቃውሟቸውን በአደባባይ እንዲያሰሙ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ተስፋለም ወልደየስ
አዜብ ታደሰ