1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከኢትዮጵያ ሞያሌ የተሰደዱት 10,557 ደረሱ

Merga Yonas Bula
ማክሰኞ፣ መጋቢት 11 2010

መጋቢት አንድ ቀን፣ 2010 ዓ/ም የመከላከያ ሠራዊት በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን ሞያሌ ከተማ ጥቃት ካደረሰ በኋላ በከተማዋና በአከባቢዉ ከሚገኙ ቀበሌዎች የተፈናቀሉት ሰዎች ቁጥር ወደ 50ሺህ እንደሚሆን የከተማዉ ከንቲባ አቶ አስቻለዉ ዮሃንስ ለዶይቼ ቬሌ መናገራቸዉ ይታወሳል።

https://p.dw.com/p/2ueKZ
Äthiopien vertriebene Moyale-Bewohner in der Oromia-Region
ምስል privat

ከቀናት በኋላ የመንግስት መገናኛ ብዙሀን የተፈናቃሉት ሰዎች 39, 825 መሆኑን ዘግበዋል። ግጭቱ ከተከሰተ ወዲህ በሽዎች የሚቆጠሩ ወደ ጎረቤት  ኬንያ ኢየተሰደዱ መሆኑን ዘገባዎች ያስረዳሉ። ወደ ኬንያ ደርሰው በቀይ መስቀል የተመዘገቡት ቁጥርም 10, 500 በላይ መሆኑን የኬንያ የቀይ መስቀል ማህበር የሕዝብ ግኑኝነትና የኮሙኒኬሼን አስተዳዳር ወ/ሮ ኖኤላ ናሙላንዳ ሙሱንድ ለዶይቼ ቬሌ አስታውቀዋል። «የስደተኞቹ ቁጥር ኢየጨመረ ይገኛል። በአሁኑ ሰዓት በኬንያ ደርሶ መመዝገብ የቻሉት ወደ 10, 557 ደርሰዋል። በእርግጥ ይህ ቁጥር በጣም እንደሚጨምር ይጠበቃል። ምክንያቱም ብዙ ሰዎች አሁንም ወደ ሀገሪቱ እየገቡ ነው።»

በአጠቃላይ የተፈናቃዮቹ ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ የተጠየቁት ናሙላንዳ ሲመልሱ: «እኛ መናገር የምንችለዉ ያረጋገጥነዉን ቁጥር ብቻ ነዉ። ብዙ ቁጥር ያላቸዉ ተፈናቃዮች ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅለዋል። በድንበር አከባቢ የምገኙት ከዘመዶቻቸዉ ጋር ኢየኖሩ ነዉ። ግን  10, 557 እኛ ያረጋገጥናቸዉ ናቸዉ። ግን አሁንም ብዙ ሰዉ እየፈለሰ ነው ። ግን እነሱ ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅለዋል።»

በአሁኑ ጊዜ በኬንያ በማርሳቢት ካውንቲ ዉስጥ ተጠሎ የሚገኙት ስድተኞች ቁጥር በሶሎሎ 4757, በሶማሬ 4910 እንድሁም በስፋ/ቡትዬ 890 መሆናቸዉን ወ/ሮ ኖኤላ ናሙላንዳ ሙሱንድ ተናግረዋል። እርሳቸው እንደሚሉት በሞያሌ ሴሲ በተባለዉ ቦታ የሚገኘዉ መጠለያ ለስደተኞቹ ተስማሚ አይደለም። ምክንያታቸዉን ሲገልፁም፣«በቦታና  በፅዳት አገልግሎት እጥረት መጠለያው ተስማሚ አይደለም። ጊዜያዊ መፍትሄ ለመፈለግ በካዉንትዉ የተቋቋመዉ ግብረ-ሃይል ስደተኞቹን በቂ ቦታ ወዳላቸው እና ሰብዓዊ ርዳታ ሊያገኙ ወደሚችሉባቸው ወደ ሌሎች መጠለያዎች እንቀሳቅሰዋቸዋል።»

መሰረታዊ የጤናና የፅዳት አገልግሎቶች ከመሰጠት ጎን ለጎን ከቤቴሴቦቻቸዉ ጋር ተለያይቶ የነበሩትን መልሶ የማገናኘት ስራ እየሰራ መሆኑን የኬንያ ቀይ መስቀል ያወጣዉ መግለጫ ያመለክታል።

ወደ ኬንያ ኢየገቡ ካሉት ዉስጥ 80 በመቶ የሚሆኑት ሴቶችና ሕጻናት መሆናቸዉን የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን ትላንት ባወጣዉ ዘገባ አስታውቋል። ወደ 1500ዎቹ  ከአምስት ዓመት እድሜ በታች መሆናቸው እና 600  ነፍሰ ጡር እናቶች እንደሆኑ ተገልጿል። የአካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን ከተሰደዱት መካከል ይገኙበታል።

የኢትዮጵያ መንግስት የተፈናቀሉትን መልሶ ለማቋቋም ጥረት ኢያደረገ መሆኑን የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ጀነራል አሰፋ አብዮ ቅዳሜ እለት ለጋዜጠኞች ማብራርያ በሰጡበት ወቅት ተናግረዋል።

መርጋ ዮናስ

ሂሩት መለሰ