1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከለገጣፎ ቤታቸው የፈረሰባቸው ወገኖች

ሐሙስ፣ የካቲት 28 2011

ከሳምንታት በፊት ከለገጣፎ ከተማ ሕገወጥ ነው በሚል ቤታቸው የፈረሰባቸው 500 ያህል አባወራዎች የሚገኙበትን ሁኔታ አሳሳቢ እንደሆነ አመለከቱ። እነዚህን ወገኖች  ወደ ተጠለሉበት በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለከተማ ወረዳ 10 በሚገኘው አያት መካነ ሕይወት መድኃኒዓለም ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ዘጋቢያችን ሰሎሞን ሙጬ ዛሬ አነጋግሯቸዋል።

https://p.dw.com/p/3Eccs
Äthiopien Vertriebene Menschen bei Legetafo
ምስል DW/Solomon Muchie

«የሰቀቀን ሕይወት እየገፋን ነው»

ለቀናት ፀሐይ እና ብርድ ሲፈራረቅብን አስቸጋሪ ሕይወት ስንመራ ነበር ያሉት እነዚህ ቤተሰቦች  የምግብ፣ የጤና፣ የህክምና እና የመጠለያ ችግር እየተፈራረቀባቸው የሰቀቀን ኑሮ እየገፉ መሆኑን ተናግረዋል። በቤተ ክርስቲያኑ ሕጻናት፣ አራስ እናቶች፣ ነፍሰጡሮች እና ሌሎችም ፈታኝ የጭንቅ ሕይወት እየገፉ መሆናቸውንና አሁን ዝናብ መዝነብ መጀመሩ ሌላ ጭንቀት እንደፈጠረባቸውም ነግረውናል፡፡ ለችግራችን መፍትሄ ፍለጋ ያልሄድንበት የለም ያሉት  DW ያነጋገራቸው ዜጎች ተስፋቸው መሟጠጡንና ሀገር አልባነት እንደሚሰማቸው ተናግረዋል፡፡ በየእለቱ ደከመኝ ሳይልና ሳይሰለች ድጋፍ እያደረገልን ያለው የአዲስ አበባ ህዝብ ምስጋና ይድረሰው ያሉት ቤት አልባዎቹ ሰዎች በፈረሰባቸው ቤት እስከ 10 አመት የሚሆናቸውን ልጆች ወልደው እንዳሳደጉበት እና በነበራቸው ጥሩ የልማት ሥራ ተሳትፎ ከለገጣፎ ከተማ አስተዳደር የምስጋና የምስክር ወረቀት ያገኙበትንም ሰነድ አሳይተውናል፡፡ መንግሥት ችግራችንን ተመልክቶ መፍትሄ እንዲያበጅልን ሲሉም ጠያቄያቸውን አቅርበዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያኑ በርከት ያሉ የፕላስቲክ ቤቶች የተወጠሩ ሲሆን በ 300 ሽህ ብር ተገዝቶ የነበረ የቤተክርስቲያኗ ትልቅ ድንኳን እና አንድ ሌላ አነስ ያለ የቀይ መስቀል ድንኳን ተዘርግቶ ሕጻናት እና እናቶች አርፈውበታል፡፡

ሰሎሞን ሙጬ

ሸዋዬ ለገሠ

ተስፋለም ወልደየስ