1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አርቲስት ፈቃዱ ተ/ማርያም እና የኢትዮጵያ ኪነጥበብ

ዓርብ፣ መጋቢት 14 2010

«”ለወገን ደራሽ ወገን ነው” በሚል ከልብ በመነጨ ፍቅር ወገናዊነታቸውን በተግባር አያሳዩ ነው:: በፀሎት ከማሰብ ጀምሮ ኩላሊታችንን መለገስ እንፈልጋለን የሚሉ እና በሀሳብም በገንዘብም የደገፉ በርካቶች ናቸው አሁንም አለሁ ባይነታችሁ ይቀጥል እግዚአብሔር ያክብርልን።»

https://p.dw.com/p/2uoFu
አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም
አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም ምስል Teworos Tessfaye

የጥበብ ስራን ከማየትና ከማድነቅ በላይ ለተጠባቢው ፍቅርና አክብሮትን የሚለግሰው ውድ ህዝብ አሁንም የጋሽ ፍቃዱን መታመም ከሰማበት ጊዜ ጀምሮ ያሳየው ወደር የሌለው የፍቅር ምላሽ እጅግ የሚያስደስት ነው። በመላው አለም የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ” ለወገን ደራሽ ወገን ነው” በሚል ከልብ በመነጨ ፍቅር ወገናዊነታቸውን በተግባር አያሳዩ ነው:: በፀሎት ከማሰብ ጀምሮ ኩላሊታችንን መለገስ እንፈልጋለን የሚሉ እና በሀሳብም በገንዘብም የደገፉ በርካቶች ናቸው አሁንም አለሁ ባይነታችሁ ይቀጥል እግዚአብሔር ያክብርልን። ይላል« በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች በሽዎች አድናቂዎቹ ወዳጆቹ ከፃፉት አስተያት አንዱ። ከትናንት በስትያ አመሻሹ ላይ «የጤና ጥበቃ ሚ/ር አርቲስት ፍቃዱ ተ/ ማርያም በነጻ ሙሉ የኩላሊት ንቅለ ተከላ በሀገር ውስጥ ማድረግ እንዲችል ፈቃድ ሰጥቷል።» የሚለዉ ዜና ኢትዮጵያዉያን ጆሮ ከደረሰ በኋላ አቤት አንድነት እና መተጋገዙ ሲያምርብን ፤ ደስ የሚል ዜና ስለፍቄ የደስታችን ተካፋይ የሆናቹ  ሼር ሼር ሼር ሲሉ ኢትዮጵያዉያኑ በተለያዩ የማኅበራዊ መገናኛዎች ደስታቸዉን አካፍለዋል አጋርተዋል። ይቺ ሼር ሼር ምንድነች እንዳትሉ ማኅበራዊ መገናኛ የወለዳት ከእንጊዚዘኛዉ ቃል የተዋሳት  አካፍሉ አሰራጩ አጋሩ  ማለት መሆኑ ነዉ እናም ዛሬ ስለ አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም ኪነጥበባዊ ስራዎች እንዲሁም ስለ ኢትዮጵያ የኪነ-ጥበባት ማኅበር ትንሽ ልንል ቅንብር ይዘናል። 

Fekadu Tekelmariam
ምስል Teworos Tessfaye

አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም ሲነሳ የብዙዎች የትያትር ፍቅር እየጎለበተ የመጣዉ በፍቃዱና እንዲሁም ከሱ ትንሽ ቀደም ብለዉ በነበሩት አርቲስት ደበበ እሸቱ ዘመን እንደሆን የተለያዩ ሰዎች አስተያየቶቻቸዉን ይገልፃሉ። አርቲስት ፈቃዱ ተክለማርያም አልጋ አልያዘም እንጂ ታሞአል መባል ሲሰማ  በተዉኔቱ መድረክ የቴድሮስን ወኔ የተቀበለዉ በሬድዮ በሚያቀርባቸዉ የተለያዩ ትረካዎች በፍቅሩ የተነደፈ ሁሉ አንድነቱን አሳየ። የቅርብ ወዳጁ የሆነዉ የብሔራዊ ትያትሩ አርቲስት ቴዮድሮስ ተስፋዬም ይህንኑ ነዉ የገለፀዉ። 

« ፍቄ በሱ ዘመን የነበሩ የትያትር ባለሞያዎች አንዳንዶች ከሃገር ወጥተዋል፤ አንዳንዶቹም ከጥበቡ ወተዋል፤ እሱ ብቻ ነዉ በዘመኑ ካሉት በሞያዉ የቀጠለዉ። የሚያከብር ጥበብን፤ እስዋ ራስዋ ጥበብ  የምታከብረዉ በሰራቸዉ ስራዎች ሁሉ የማይኩራራ ክብሩን ከትንሽ እስከትልቅ የሚገልፅ ፤ ደከመኝ ሰለቸኝ የማይል፤ ሕዝብ በጠራዉ ቦታ የሚገኝ ሞያዉን የሚወድና ሰዉን

ሚወድ ፤ ቤተሰቡን የሚወድ ሰዉ ነዉ ፈቃዱ። ሌላዉ በጣም ያስደነቀን ነገር፤ የሕዝብ ፍቅርን በቁሙ ማየቱ በጣም በጣም ያስደነቀን ነዉ። ፍቃዱ የኪነ-ጥበቡ አርማ ነዉ» 

Fekadu Tekelmariam
ምስል Teworos Tessfaye

በመድረክ ላይ በአብዛኛዉ በንግሥናዉ አልያም ደግሞ አፄ ቴዮድሮስን ሆኖ ነዉ የሚታወቀዉ። ይህን በተመለከተ ከመድረክ ጀርባ፤ ንጉሱ እንደሚባባሉ የስራ ባልደረባዉና ባልንጀራዉ አርቲስት ቴዮድሮስ ተስፋዬ ገልፆአል። በአርቲስት ፈቃዱ ተክለማርያም ንግሥና ሌላዉ ታዋቂና ተወዳጁ የመድረክ ንጉስ ደበበ እሸቱም ይስማማል።

«የተደረገዉ መነሳሳት እኔን ብቻ ሳይሆን መላዉን የጥበቡን ቤተሰቦች እና ኢትዮጵያዉያንን ሁሉ ያስደሰተ ነገር ነዉ። ምክንያቱም በአጭር ጊዜ ዉስጥ ሕዝቡ ከፍተኛ ርብርብ አድርጓል። ፍቃዱ እስከዛሬ በመድረክ ሞያዉ ላይ ያደረገዉን አስተዋፅኦ በተመለከተ ሕብረተሰቡ ምላሽ እየሰጠ ይመስለኛል። ፍቅሩን እየገለፀበት ነዉ። ይሄ ደግሞ ለፍቃዱ የተደረገ ብቻ ሳይሆን ለሁላችንም እንደተደረገ አድርጌ ነዉ የማየዉ።»  

የፀፀት ፊልም ደራሲና በአሁኑ ወቅት ለንደን የኢትዮጵያ ቅርፅ ማበልጸግያ ማኅበር ሊቀመንበር አቶ አለባቸዉ ደሳለኝ፤ ኢትዮጵያ ሳሉ ከአርቲስት ፈቃዱ ተክለማርያም ጋር ሰርተዋል። በፀፀት ፊልም ላይም ፍቃዱ ተክለማርያም ዳኛ ሆኖ ተዉኖአል።

ሌላዋ የአርቲስት ፈቃዱ አድናቂና ጓደኛ የአቤኔዘር ፕሮሞሽን መስራች እና በሃገረ ሰሜን አሜሪካ ከታዋቂዉ ገጣሚ ከኢሳያስ ልሳኑ ጋር የኢትዮ ዲያስፖራ ሬድዮ አዘጋጅዋ ቅድስት ተስፋዬ ወይም ቅድስት አቤኔዘር ናት።   

ኢትዮጵያዉያን የጥበብ ሠራተኞች ጥበብን በመድረክ ከማቅረብ በስተቀር የራሴ የሚሉት ኃብት አለማትረፋቸዉ በተለይ ደግሞ ጠቢባኑ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ የአንድ ሰሞን ወሪ ሆኖ መረሳቱ በችግር የሚኖሩትን ለሞያዉ ተገዥ የሆኑትን የጥበቡን ባለሞያዎች ያስከፋ መሆኑ ተሰምቶአል። በርግጥ ጠቢባኑ ማኅበር የላቸዉንምን? አርቲስት ደበበ እሸቱ እንደሚለዉ አለም የለምም ማለት ይቻላል።  

አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም
አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም ምስል Teworos Tessfaye

«አለም የለምም ማለት ይቻላል ሁለት ሦስት ማኅበር ይኖራል እንዲህ አይነቱ ችግር እኛም ጋር እየገባ ነዉ። የሚመለከታቸዉም የማይመለከታቸዉም ማኅበር ይከፍታሉ። ግን ለጥበቡ ባለሞያዎች ምንም የሚያደርጉላቸዉ አልያም የሚጠቅሙአቸዉ ነገር የለም። አሁንም ትናንትም ነገም ተነጎድያም አርቲስት ሲታመም በልመና ነዉ የሚታከመዉ። በድረሱልን ጥሪ ነዉ የሚጮኸዉ። እንደ ወጉ እንደ ማዕረጉ ቢሆን ኖሮ የራሳችን ብቻ ሳይሆን ሌላዉንም ሊያወጣ የሚችል ሞያ ነበር ያለዉ። ግን አላሰብንበትም። በጥንቃቄ አልተደራጀንም። ማኅበር አለም የለም የሚባልበት ደረጃ ነዉ እንጂ፤ አለ ብዩ አፌን ሞልቼ መናገር አልችልም።»   

አንዱ ችግራችን በጋራ አለመሰባሰባችን ነዉ ያለዉ አርቲስት ቴዮድሮስ ተስፋዬ በበኩሉ፤ የተለያዩ ማኅበራት በየወሩ ገንዘብ ከመሰብሰብ በስተቀር ለጥበቡ ባለሞያና ለሞያዉ የፈየዱት ነገር የለም።

Äthiopien National Theater feiert 60-jähriges Jubiläum Tekle Desta
ምስል Tekle Desta

የኛ ጠቢባን ጥበብን ነዉ ይዘዉ የወጡት ያለችን፤ በሰሜን አሜሪካ የኢትዮ ዲያስፖራ ሬድዮ አዘጋጅዋ ቅድስት ተስፋዬ በበኩልዋ ባለሞያዎቹ ከሃብት ይልቅ የሕዝብ ፍቅር እንዳላቸዉ ተናግራለች።  

አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም ላለፉት 42 ዓመታት በመድረክ፣ በሬዲዮ፣ በቴሌሺዥን እና አሁን ደግሞ በፊልም በርካታ የመድረክ ጥበብን ተጫዉቷል። ፍቃዱ በተለይ ከሚታወቅባቸዉ ተውኔቶች መካከል ፤ ኦቴሎ፣ ኤዲፐስ ንጉሥ፣ ሐምሌት፣ ቴዎድሮስ፣ ንጉሥ ኦርማህ፣ መቃብር ቆፋሪውና የሬሣ ሳጥን ሻጩ፣ የሰርጒ ዋዜማ፣ አቡጊዳ ቀይሶ፣ ባለካባ ባለዳባ፣ መልዕክተ ወዛደር ተጠቃሽ ሲሆኑ ፤ ፍቃዱ ተክለማርያም  በቴሌቪዥን ከተወናቸው መካከል ያልተከፈለ ደግሞ ኦዳ፣ ያበቅየለሸ ኑዛዜ፣ ባለጉዳይ እና የመሳሰሉት በህዝብ ዘንድ ተወዳጅነትን አትርፈዉለታል። ፍቃዱ “መጽሃፍት ዓለም” ይባል በነበረው የሬዲዮ ፕሮግራም “ሞገደኛው ነወጤ፣ ጥቁር ደም፣ ሳቤላ፣ የነበረው እንዳልነበር” የተባሉትን አጭርና ረጅም ልቦለዶችን ተውኔታዊ መልክ በመስጠት ቀልብን በሚይዝ የአተራረክ ስልት አቅርቧቸዋል፡፡ ፍቃዱ በፊልም ሥራዎች ላይ ታዋቂነትን እያተረፈ መሆኑም ይታወቃል።

ሙሉ ቅንብሩን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን እንዲከታተሉ እንጋብዛለን

አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሰ