1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አማራ ክልል ሁለት ተገደሉ፣ አራት ታገቱ

ረቡዕ፣ የካቲት 17 2013

በአማራ ክልል ምዕራብ ጎንደር ዞን መተማ ወረዳ ታጣቂዎች ፖሊስ ገድለው ሌሎች ሰላማዊ ሰዎች ማገታቸውን የአካባቢው ነዋሪዎችና ባለስልጣናት አስታውቀዋል። ከታጣቂቆቹ  ወገንም እንድ ሰው መገደሉ  ተሰምቷል። መንግስት “አፋጣኝ እርምጃ አልወሰደም” “ዘላቂ መፍትሔም አላመጣም” በሚል  አሽከርካሪዎች ከገንዳ ውሀ የትራንስፖርት አገልግሎት አቋርጠዋል።

https://p.dw.com/p/3po11
Äthiopien Verwaltungsbüro Metema woreda
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

በአማራ ክልል ታጣቂዎች የፖሊስ አባል ገደሉ

በአማራ ክልል ምዕራብ ጎንደር ዞን መተማ ወረዳ ታጣቂዎች ፖሊስ ገድለው ሌሎች ሰላማዊ ሰዎች ማገታቸውን የአካባቢው ነዋሪዎችና ባለስልጣናት አስታውቀዋል። ከታጣቂቆቹ  ወገንም እንድ ሰው መገደሉ  ተሰምቷል። መንግስት “አፋጣኝ እርምጃ አልወሰደም” “ዘላቂ መፍትሔም አላመጣም” በሚል  አሽከርካሪዎች ከገንዳ ውሀ ወደ ሽንፋና ቋራ ከተሞች  የሚሰጡትን የትራንስፖርት አገልግሎት አቋርጠዋል።  በሌላ በኩል  ወንጀለኞችን ለማደን በሚደረገው ጥረት ህብረተሰቡ አጋዥ እንዲሆን የዞኑ አስተዳደር ጠይቋል፡፡

ቀደም ባሉት ጊዜያት በማዕከላዊ ጎንደርና ምዕራብ ጎንደር ዞኖች መኪና በማስቆም የሚዘርፉ፣ የሚያግቱና ገንዘብ የሚጠይቁ ታጣቂዎች እንደነበሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ያስታውሳሉ፣ ድርጊቱ ለተወሰነ ጊዜ ቆሞ የነበረ ቢሆንም ትናንት ጠዋት  በምዕራብ ጎንደር ዞን መተማ ወረዳ ሽንፋ ከተባለች አነስተኛ ከተማ ወደ ገንዳ ውሀ ሲጓዝ የነበረን መኪና ልዩ ስሙ “ጉባዔ” ከተባለ ቦታ ላይ ታጣቂዎች አስቁመው 4 ተሳፋሪዎችን ማገታቸውን አንድ የአካባቢው ነዋሪ ለዶይቼ ቬለ በስልክ ተናግረዋል፣  “በወቅቱ በነበረ የተኩስ ልውውጥ ከታጣቂዎች ወገን አንድ ሲገደል አንድ የመንግስት የፀጥታ ባልደረባም ህይወቱ አልፏል“ ብለዋል፡፡መንግስት በተደጋጋሚ ለሚደርሱ ተመሳሳይ ችግሮች አፋጣኝ መፍትሔ መስጠት ባለመቻሉ ህብረተሰቡ ቅሬታውን በተለያዩ መንገዶች እየገለፀ ሲሆን አሽከርካሪዎች ከትናንት ጀምሮ ከገንዳ ውሀ ወደ ሽንፋና ቋራ የሚሰጡትን የትርንስፖርት አገልግሎት ማቋረጣቸውን እኚሁ አስተያት ሰጪ ተናግረዋል፡፡የምዕራብ ጎንደር ዞን አስተዳዳሪ አቶ ደሳለኝ ጣሰው በበኩላቸው ጥቃቱ ትናንት መፈፀሙን አመልክተው በነበረው የተኩስ ልውውጥ ከሁለቱም ወገን የአንድ፣ አንድ  ህይወት ማለፉንን አረጋግጠዋል፣ ከየትኛውም ወገን የቆሰለ ግን የለምም ሲሉ መልሰዋል፡፡የዚህ ዓይነት ችግሮች መፈጠራቸው አዲስ ነገር እንዳልሆነ ያመለከቱት አቶ ደሳለኝ መንግስት ለጉዳዩ ትኩረት አልሰጠውም የሚለውን ግን አይቀበሉም፡፡ የፀጥታ ኃይሉ ወደ ቦታው መሰማራቱን አመልክተዋል፡፡የትራንስፖርት አገልግሎትን በማቋረጥ መፍትሔ አይመጣም ያሉት ዋና ህብረተሰቡ ይልቁንም መረጃ በመስጠት ከፀጥታ ኃይሉ ጎን እንዲሰለፍ ጠይቀዋል፡፡በሌሎች አካባቢዎች ያሉ አሽከርካሪዎችም በተደራጁ ዘራፊዎች ጥቃት እየደረሰብን ነው ሲሉ ቅሬታ ያሰማሉ፡፡ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድ አሽከርካሪ ዛሬ ከባሕር ዳር ቅርብ እርቀት ላይ በምትገኝ ዘንዘልማ በተባለች አቅራቢያ የሌላ የጭነት መኪና ሸራ ተቀድዶ የዝርፊያ ሙከራ እንደተደረገ ነግረውናል፡፡

አለምነው መኮንን

ታምራት ዲንሳ

ኂሩት መለሰ