1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቪሊ ብራንት የጀርመንን ታሪክ ያደሱበት ቅጽበት

ማክሰኞ፣ ኅዳር 29 2013

ቪሊ ብራንት የዛሬ 28 ዓመት ቢያልፉም ከ50 ዓመት በፊት በፈጸሙት ያልተጠበቀ አኩሪ ተግባር ዘወትር ስማቸው ይነሳል።ለጉብኝት በሄዱበት ዋርሶ በናዚ ጀርመን ለተጨፈጨፉ አይሁዳውያን መታሰቢያ በጎርጎሮሳዊው ታህሳስ 7፣ 1970 የአበባ ጉንጉን ካስቀመጡ በኋላ ድንገት ከሐወልቱ ፊት ለፊት ተንበረከኩ።ይህ ያልተጠበቀ ድርጊታቸው የጀርመንን ታሪክ ቀየረ።

https://p.dw.com/p/3mRfZ
Warschau Kniefall Willy Brandt vor Mahnmal im einstigen jüdischen Ghetto
ምስል CAF/AFP

ቪሊ ብራንት የጀርመንን ታሪክ ያደሱበት ቅጽበት

ጎርጎሮሳዊው ታህሳስ 7 1970 በአዲሱ የጀርመን ታሪክ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ቀን ነው።በዕለቱ የያኔው የጀርመን መራሄ መንግሥት ቪሊ ብራንት ለጉብኝት በሄዱበት የፖላንድ ዋና ከተማ ዋርሶ በናዚ ጀርመን የሰዎች ማጎሪያ ለተገደሉ አይሁዳውያን መታሰቢያ በተሰራ ሐውልት ፊት ለፊት ድንገት ሳይታሰብ መንበርከካቸው የሃገራቸውን ታሪክ አድሷል። 
ከጎርጎሮሳዊው 1964 እስከ 1974 የጀርመን መራሄ መንግሥት የነበሩት ቪሊ ብራንት በጎርጎሮሳዊው ታህሳስ 18፣1913 ሲወለዱ የወጣላቸው ስም ሄርበርት ኤርንስት ካርል ፍራህም ነበር።  በናዚ ጀርመን የአገዛዝ ዘመን ኖርዌይና ስዊድን የተሰደዱት ግራ ዘመሙ ጋዜጠኛ ከናዚዎች ክትትል ለማምለጥ፣ያኔ ለራሳቸው የሰጡት ስም ነው ቪሊ ብራንት።በ1948 ይህን ስማቸውን በይፋ ተቀበሉት።እኚህ የጀርመን ሶሻል ዴሞክራት ፖለቲከኛ የዛሬ 28 ዓመት ቢልፉም ከ50 ዓመት በፈጸሙት ያልተጠበቀ አኩሪ ተግባር ዘወትር ስማቸው ይነሳል።ብራንት ለጉብኝት በሄዱበት ዋርሶ በናዚ ጀርመን ለተጨፈጨፉ አይሁዳውያን መታሰቢያ በጎርጎሮሳዊው ታህሳስ 7፣ 1970 የአበባ ጉንጉን ካስቀመጡ በኋላ ከመቅጽበት ከሐወልቱ ፊት ለፊት ተንበረከኩ።ይህ ያልተጠበቀ ድርጊታቸው በናዚዎች የጠለሸውን የጀርመንን ታሪክ ቀየረ።የያኔውን የምሥራቅና ምዕራብ ልዩነት አጥብቦ ለጀርመን ውህደት መሠረት ጣለ።ከጀርመን አልፎም ለዓለም ብዙ አስተዋጽኦ አበረከተ። የአፍሪቃና የመካከለኛው ምሥራቅ ጉዳዮች አማካሪና ፀሐፊ እንዲሁም አንጋፋው የታሪክ ምሁር ዶክተር ልዑል አስፋወሰን አሥራተ ካሳ ናቸው ትናንት 50ኛ ዓመቱ የታሰበው፣የብራንት ቅጽበታዊ ውሳኔ ያስገኛቸውን ጥቅሞች በጥቅሉ አስረድተዋል።ቪሊ ብራንት ይህን ዓለምን ያስደመመ ተግባር ሲፈጽሙ በስፍራው የነበሩ የጀርመን ሚኒስትር ድርጊቱ በርሳቸውና በሌሎች ላይ የፈጠረውን ስሜት በአንድ ወቅት እንዳጋሯቸው ዶክተር አስፋወሰን ያስታውሳሉ። በታሪክ ትልቅ አክብሮት የተቸረው የብራንት ቅጽበታዊ ውሳኔ በጀርመናውያን ዘንድ የተለያየ  ስሜት ነው የፈጠረው።ብራንት ዝቅ ብለው በሐውልቱ ፊት ለፊት መንበርከካቸው ዶክተር ልዑል አስፋወሰን አስራተ እንደተናገሩት ያስደሰታቸው እንዳሉ ሁሉ በእጅጉ የተከፉና አገራቸውን አሳልፎ በመስጠት የፈረጇቸውም ጀርመናውያን ነበሩ ።  ቪሊ ብራንት የዛሬ 50 ዓመት ዋርሶ ፖላንድ ሳይታሰብ ተንበርክከው የሃገራቸውንም የዓለምንም ታሪክ የቀየሩበት አጋጣሚ ብዙ መልዕክቶችን አስተላልፏል።

Asfa-Wossen - deutschsprachiger Autor und Unternehmensberater
ምስል picture-alliance/dpa/E. Elsner

ኂሩት መለሰ

አዜብ ታደሰ