1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ወንድወሰን መርዓዊ

ዓርብ፣ ጳጉሜን 3 2009

የዛሬው የወጣቶች ዓለም እንግዳችን ከጫማ ጠራጊነት ተነስቶ፣ የንግድ ሱቅ ከፍቶ ራሱን ለመቻል በመፍጨርጨር ላይ እያለ፤ በተተመነበት የቀን ገቢ ግብር ምክንያት ሱቁን ዘግቶ ለመቀመጥ የተገደደ የ 25 ዓመት ወጣት ነው።

https://p.dw.com/p/2jWpt
Äthiopien Jimma Geschlossene Geschäfte
ምስል DW User via Whatsapp

ወንድወሰን መርዓዊ

ወንድወሰን መርዓዊ ኢትዮጵያ ውስጥ የተተመነባቸውን የዕለት ገቢ ግብር መክፈል ከማይችሉ ነጋዴዎች አንዱ ነው። በደብረ ታቦር ከተማ ነዋሪ የሆነው ወጣት የኤሌክትሮኒስክስ መጠገኛ ሱቅ የከፈተው በ 2008 ዓም መጨረሻ ላይ ነው። ሱቁን እንዲከፍት የተባበሩት ደግሞ ጓደኞቹ እና የሚያውቁት ሰዎች ናቸው። ወንድወሰን ወደሥራው ዓለም ገብቶ ራሱን ማስተዳደር የጀመረው ግን ገና በልጅነቱ ነው። « ሙሉ እድሜውን ሊስትሮ እየሰራው ጎዳና ላይ ነው ያሳለፍኩት» ይላል። ወንድወሰን የልጅነት ጊዜውን የሚያስታውሰው በሥራ ነው። እንደ ሌሎች፤ ልጅ ብቻ ሆኖ፤ ለማደግ አማራጭ አልነበረውም። አባቱን አያውቅም እናቱ በሞት ስትለየው ነው ለጎዳና የተዳረገው።ዕጣ ፈንታውን ተቀብሎ ከእጅ ወደ አፍ በሆነ ኑሮው ራሱን እያስተዳደረ ያደገዉ ወንድወሰን ታድያ ዛሬ ሳይፈልግ ሥራ ፈት ሆኗል። በግብር ምክንያት። በግማሽ ከተስተካከለም በኋላ 14390 ብር ግብር ክፈል ተብሏል። ወንድወሰን ሱቅ ውስጥ ያለው ንብረት ቢገመት 3,500 ብር ገደማ እንደሚሆን ይናገራል።  በጥሬ የነበረኝ 1,500 ብርም ሱቄን ከዘጋሁ በኋላ በልቶ ማደሪያዬ ሆኗል ይላል። የተጠየቀውን ገንዘብ ከየት እንደሚቆፍር ግራ ገብቶታል።

Äthiopien Jimma Geschlossene Geschäfte
የተለያዩ የንግድ ተቋማት ባለቤቶች ባለፉት ሁለት ወራቶች ሱቃቸውን እየዘጉ ተቋውሞዋቸውን አሰምተዋል።ምስል DW User via Whatsapp

ሱቁን ዘግቶ የተቀመጠው ወንድወሰን ብቻ አይደለም። ሁኔታው ያበሳጫቸው የተለያዩ የንግድ ተቋማት ባለቤቶች ባለፉት ሁለት ወራቶች ሱቃቸውን እየዘጉ ተቋውሞዋቸውን አሰምተዋል። በተለይ የኦሮምያ እና የአማራ ክልል ከተሞች በርካታ የሥራ ማቆም የአድማ ቀናትን አስተናግደዋል። የኢትዮጵያ መንግስሥት «ሐ» የሚል ደረጃ በሰጣቸዉ አነሰተኛ ነጋዴዎች ላይ የጣለዉ የግምት ግብር ተመን ከአቅማችን በላይ ነው፣ ትክክል አይደለም እያሉ ነጋዴዎች ያሰሙት ቅሬታ ተሰሚነት ያገኘው ግን በቅርቡ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማሪያም ደሳለኝ ነሐሴ 14 ቀን 2009 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ላሊበላ አዳራሽ እንደተናገሩት« በመረጃ፣ በግንዛቤ እጥረት እና ሌብነት ምክንያት ወደ 40/100 የሚጠጋው የቀን ገቢ ግብር ትመና ችግር እንዳለበት ታውቋል።

ስህተቱ ተመርምሮ ወንደሰን እና መሰሎቹ መፍትሄ እስኪያገኙ ድረስ የሚፈጀው ጊዜ ግልፅ አይደለም። ራሱን ችሎ ለመኖር እየተፍጨረጨረ የነበረው ወጣት ዛሬ ሥራውን ብቻ ሳይሆን ያጣው ትምህርቱንም ለማቋረጥ ተገዷል። ዘንድሮ ወደ ዘጠነኛ ክፍል አልፎ የነበረው ወንድወሰን ትምህርቱን በተለያዩ ምክንያቶች በየጊዜው ለማቋረጥ የተገደደ ቢሆንም ለአጭር ጊዜም ቢሆንም መተዳደሪያው የሆነው የኤሌክትሮኒክስ ጥገና ስልጠናን ለማግኘት ብዙ መስዋዕት እንደከፈለ ይናገራል።

ልደት አበበ

ሸዋዬ ለገሰ