በድሬደዋ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት ለተጎጂዎች ድጋፉን ገለፀ
ማክሰኞ፣ ኅዳር 28 2014ዘጠኝ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ያካተተው በድሬደዋ የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት በሀገሪቱ ባለው ጦርነት ሳቢያ በአማራ እና አፋር ክልሎች ለተፈናቀሉ ወገኖች እና የመከላከያ ሰራዊቱን ለመደገፍ የበኩላቸውን እንደሚሠሩ አስታወቁ፡፡ በተለይ ለተፈናቃዮች የአልባሳት እና ሌሎች ድጋፎችን የማሰባሰብ ሥራ ቀደም ብለው ሲሰሩ መቆየታቸውን የተናገሩ የፖሊቲካ ፓርቲዎች በቀጣይም በጋራ ምክር ቤቱ ተቀናጅተው የሚጠበቅባቸውን እንደሚወጡ ገልፀዋል፡፡ ገዢው ብልፅግናን ጨምሮ ዘጠኝ የፖሊቲካ ፓርቲዎችን ያካተተው በድሬደዋ የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ዮናስ በትሩ ባቀረቡት የጋራ ምክር ቤቱ መግለጫ መንግሥት በአሸባሪነት የፈረጀው ህወሓት በከፈተው ጦርነት በአፋር እና አማራ ክልሎች ህዝብ ላይ የደረሰውን መፈናቀል በማውገዝ ከህዝባችን እና ከመርያችን ጎን በመቆም የሀገር ሉአላዊነትንና አንድነትን ለማስጠበቅ ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡
በጋራ ምክር ቤቱ የተሰባሰቡ ፖለቲካ ፓርቲዎች ለሀገር መከላከያ ሠራዊት እና በአማራ እና አፋር ክልሎች ለተፈናቀሉ ዜጎች ድጋፍ የማሰባሰብ ሥራ በመስራት ደጀንነታችንን እናረጋግጣለን ብለዋል፡፡ በድሬደዋ የኢህአፓ ፓርቲ ተወካይ አቶ ወንደሰን ዘለቀ ቀደም ሲል ለተጎጂ ወገኖች የሚሆን አልባሳት እና ሌሎች ቁሳቁሶችን የማሰባሰብ ሥራ ሲሰሩ መቆየቱን ገልፀው በቀጣይም ይህንኑ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል።
የጋራ ምክር ቤቱ አባል የሆኑ ሌሎች የፖሊቲካ ፓርቲዎችም በጦርነቱ ተጎጂ ለሆኑ በአማራ እና አፋር ክልል የሚገኙ ዜጎች አስፈላጊ የሆነውን ድጋፍ በሚገኙበት አካባቢ ያለውን ኅብረተሰብ በማስተባበር ለመሰብሰብ እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ተናግረዋል። ድሬደዋ የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ተጎጂዎችን ከመርዳት ባለፈ የአካባቢ ሰላምን በማስጠበቅ፣ የዘማች ቤተሰቦችን መደገፍ እና ሌሎች ተግባራትን ከመንግሥት ጎን በመሆን እንደሚያከናውኑ አስታውቀዋል።
መሳይ ተክሉ
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሺ