በኦሮሚያ የመንግሥት ባለስልጣናትና ፀጥታ ኃይሎች መታሠር
ሐሙስ፣ መጋቢት 6 2010በዛሬዉ ዕለትም የኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ የኮሙኒኬሼን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ታዬ ደንደኣ መታሰራቸዉ ተሰምቷል።
ባሳለፍነዉ ቅዳሜ በክልሉ በቦረና ዞን በሞያሌ ከተማ የአገሪቱ መከላክያ ስራዊት «በተሳሳተ መረጃ» ላይ ተመስርቶ ወሰደዉ የተባለዉ ርምጃ ለብዙ ዜጎች ሕይወት ማለፍ ምክንያት መሆኑ ተገልጿል። የፍትሕ ቢሮ ቃል አቀባዩ አቶ ታዬ ደንዳኣ ይህን አስመልክቶ ዶቼ ቬለን ጨምሮ ለተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ድርጊቱ ሆን ተብሎ እንደተፈጸመ እና ፈፃሚዎቹም ሆኑ ትዕዛዝ ሰጪዎቹ ሕግ ፊት መቅረብ እንደሚኖርባቸዉ ገልጸዋል።
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መመርያ ከኮማንድ ፖስቱ «ፍቃድ ውጭ በጸጥታ ጉዳይ ላይ የፌደራል መንግሥት፣ የክልል አካል ወይም ኃይል በህዝብ ይፋ የሚሆን መግለጫ መስጠት» እንደማይችሉ ይጠቅሳል። ኮማንድ ፖስቱ እየወሰደ ያለዉ የእስራት እርምጃ ላይ ይፋዊ ምክንያት ባይሰጥም ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉት ለአቶ ታዬና ለሌሎች ባለስልጣናት መታሰር መመርያዉ እንደምክንያት ሊቀርብ እንደምችል ይናገራሉ።
አቶ ታዬ ዳንዳኣ በኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ ቃል አቀባይ ሆነው ከመሾማቸዉ አስቀድሞ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር አባል ነህ በሚል ተከሰው ለ10 ዓመታት በእስር ቆይተዋል። አቶ ታዬን ጨምሮ ሌሎች የታሰሩበትን ምክንያትም ሆነ የሰብዓዊ መብት አያያዛቸዉ ላይ የበለጠ መረጃ ለማግኘት ወደ ኮማንድ ፖስቱ ሴክሬታርያትም ሆነ የአጣሪ ቦርዱ አባላት ጋር ደጋግመን ብንደውልም አልተሳካልንም።
ሙሉ ዘገባዉን ለማዳመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።
መርጋ ዮናስ
ሸዋዬ ለገሠ