1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በትግራይ ሰብዓዊ እርዳታ እንዴት ማድረስ ይቻላል?

እሑድ፣ ሐምሌ 4 2013

በትግራይ ውጊያ ሳቢያ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የክልሉ ነዋሪ ለከፋ የምግብ እጦት መጋለጡን የግብረ ሰናይ ድርጅቶች አስታውቀዋል። ይኸ ውይይት ዕርዳታ ለትግራይ እንዴት ማቅረብ ይቻላል? ሲል ያጠይቃል። የግጭት ትንተናና አፈታት ባለሙያው ዓለማየሁ ፈንታው፣ የፖለቲካ ተንታኙ ሰላሐዲን እሸቱና በቪየና የዲፕሎማሲ ትምህርት የሚከታተሉት ሞገስ ዘውዱ ተሳትፈዋል

https://p.dw.com/p/3wIF7
Bildergalerie Äthiopien | Flucht aus der Region Tigray
ምስል Baz Ratner/REUTERS

እንወያይ፦ በትግራይ ሰብዓዊ እርዳታ እንዴት ማድረስ ይቻላል?

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ባለሥልጣናት ላለፉት ስምንት ወራት ጦርነት ባመሳቀለው የትግራይ ክልል 400 ሺሕ ገደማ ሰዎች ጠኔ ተብሎ የሚጠራው የከፋ ረሐብ እንደተጋረጠባቸው ይፋ አድርገዋል። በጸጥታ ጥበቃው ምክር ቤት በተደረገ ውይይት ላይ ንግግር ያደረጉት የድርጅቱ የአስቸኳይ ዕርዳታ አስተባባሪ እንዳሉት ሌሎች 1.8 ሚሊዮን ሰዎች በዚያው በትግራይ በጠኔ አፋፍ ላይ ይገኛሉ።

የግብረ-ሰናይ ድርጅቶች በትግራይ ሥራቸውን እንዲያከናውኑ የኢትዮጵያ መንግሥት እንደሚያመቻች ፤ ኤሌክትሪክ እና ኮምዩንኬሽን የመሳሰሉ መሠረታዊ አገልግሎቶች በአፋጣኝ ሥራ እንደሚጀምሩ ጠቅላይ ምኒስትር ዐቢይ አሕመድ ማረጋገጫ እንደሰጧቸው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አርብ ሐምሌ 02 ቀን 2013 ዓ.ም. በቃል አቀባያቸው ስቴፈን ዱጃሪች በኩል ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ከትግራይ መውጣቱ ከተገለጸ በኋላ መንግሥት ከሰኔ 21 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ በተናጠል "ሰብዓዊ የተኩስ አቁም" አውጇል።  መቐለን የተቆጣጠሩት ኃይሎች በአንፃሩ የተኩስ አቁሙን በመርኅ ደረጃ ተቀብለው ሰባት ቅድመ ሁኔታዎች አቅርበዋል።

የኢትዮጵያ መንግሥት እርዳታ በአዉሮፕላን ወደ ትግራይ እንዲጓጓዝ ፈቅዷል። የዓለም የምግብ መርሐ-ግብር 900 ሜትሪክ ቶን ምግብ፣ ነዳጅ፣ የተመጣጠነ ምግብ፣ የንጽህና መጠበቂያዎች እና የመጠለያ ግብዓቶች የጫኑ 50 ተሽከርካሪዎች ወደ ትግራይ በመጓዝ ላይ መሆናቸውን እሁድ ሐምሌ 04 ቀን 2013 ዓ.ም. አስታውቋል።

ይኸ ውይይት አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ እንዴት የሰብዓዊ ዕርዳታ ለትግራይ ማቅረብ ይቻላል? የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጫና ቀውሱን ለመፍታት ምን አይነት ሚና ይኖረዋል? የሚሉ ርዕሰ-ጉዳዮችን ይዳስሳል።

የግጭት ትንተና እና አፈታት ባለሙያው አቶ ዓለማየሁ ፈንታው፣ የፖለቲካ ተንታኙ አቶ ሰላሐዲን እሸቱ እና በቪየና የዲፕሎማሲ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙት አቶ ሞገስ ዘውዱ በውይይቱ ተሳትፈዋል። በዚህ ውይይት ላይ የሰላም ሚኒስቴር ተወካዮች እንዲሳተፉ ዶይቼ ቬለ ግብዣ ቢያቀርብም መልስ አላገኘም። ውይይቱ የተካሔደው ሐሙስ ሐምሌ 01 ቀን 2013 ዓ.ም. ነው።

ሙሉ ውይይቱን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ

እሸቴ በቀለ