በሶማሌ ክልል የተከሰተው ድርቅ ያስከተለው ጉዳት
ቅዳሜ፣ ጥር 7 2014ወቅቱን የጠበቀ የክረምት እና በልግ ዝናብ በተገቢው መልኩ አለመዝነቡን ተከትሎ በሶማሌ ክልል ዘጠኝ ዞኖች በተከሰተው ድርቅ ከሁለት መቶ ሺህ በላይ እንስሳት ሲሞቱ ከ2.5 ሚሊየን በላይ ህዝብ ለረሀብ እና የከፋ ጉዳት መዳረጉን የክልሉ መንግስት ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ገለፀ። የክልሉ መንግስት እና ሌሎች ለጋሽ ድርጅቶች ለተፈጥሯዊው ጉዳት የበኩላቸውን ጥረት እያደረጉ ቢሆንም ችግሩ ዝናብ እስቂጥል ባሉ ቀጣይ ወራት ጭምር አሳሳቢ በመሆኑ ሁሉም የበኩሉን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።
የሶማሌ ክልል መንግስት የኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ፈርሀን ጅብሪል ለዶይቼ ቬሌ በስልክ እንደገለጡት በክልሉ ዘጠኝ ዞኖች የተከሰተው ድርቅ ከሁለት መቶ ሺህ በላይ እንስሳትን ሲገድል ከ2.5 ሚሊየን በላይ ህዝብ ለከፋ ችግር እንዲጋለጥ አድርጓል።
የዝናብ በወቅቱ አለመዝነብን ተከትሎ የተከሰተው ድርቅ በእንሳስት እና በሰዎች ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ለመቀነስ በክልሉ መንግስት የተለያየ ጥረት እየተደረገ ነው ያሉት ኃላፊው በዚህም እስካሁን በሰው ህይወት ላይ የደረሰ ጉዳት የለም ብለዋል። የክልሉን ድርቅ በሚመለከት በቅርብ በተለይም በፎቶ ግራፍ እየታዩ ያሉ መረጃዎች አስከፊ ስለመሆናቸው እና ችግሩን መንግስት በትክክል ስለማንሳቱ ከDW የተጠየቁት አቶ ፈርሀን መልስ ሰጥተዋል።
ከቀናት በፊት የድሬደዋ እና የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድሮችን ጨምሮ በሌሎች አካላት እየተደረጉ ላሉ ድጋፎች ምስጋና ያቀረቡት አቶ ፈርሀን ተፈጥሯዊ በሆነ ችግር ውስጥ ላለው ህብረተሰብ ሁሉም የበኩሉን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።
በሶማሌ ክልል የተከሰተውን ድርቅ ለመቋቋም የካፒታል ፕሮጀክቶችን በጀት ጭምር ለድርቅ መከላከል ስራው እያዋለ ያለው የክልሉ መንግስት አሳሳቢ ለሆነው ድርቅ መፍትሄ ለማምጣት ቁርጠኛ አመራር ከመስጠት ባለፈ ከተለያዩ አለም አቀፍ እና ሀገር አቀፍ ለጋሽ ድርጅቶች ጋር ለመስራት ጥረት እያደረገ መሆኑ ተገልጿል።
መሳይ ተክሉ
ታምራት ዲንሳ